Monday, July 23, 2012

ጊዜዬ ገና አልደረሰም -የዮሐንስ ወንጌል የ32ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.7፡1-9)!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  በእነዚህ ምክንያት ሞት ወደ ዓለም ገብቷልና ከቅንዐትና ከምቀኝነት የባሰ ክፉ ነገር የለም፡፡ “በዲያብሎስ ቅንዐት ሞት መጣ፤ ወደዚህ ዓለምም ገባ” ተብሎ እንደተጻፈ የሰው ልጅ በክብርና በልዕልና ቢያየው ዲያብሎስን ቅንዐት ውስጥ ከቶታል፤ እርሱን ለመመቅኘትም ዓቅሙን ሁሉ ተጠቅሟል /ጥበብ 2፡24/፡፡ ይህ ቅንዐት በሰው ልጆችም ተመሳሳይ ፍሬ ሲያፈራ እናስተውላለን፡፡ ከቅንዐት የተነሣ አቤል ተገድሏል፤ ዳዊት ለሞት ተቃርቦ ነበር፤ ሌሎች ብዙ ንጹሐን ቅዱሳንም መከራ ተቀብለውበታል፡፡ በዚሁ ቅንዐት አይሁድ ክርስቶስን ገድለውታል፡፡ ወንጌላዊው ይህን ሲያስረዳ፡- “ከዚህም በኋላ ኢየሱስ አይሁድ ሊገድሉት ይፈልጉ ስለ ነበር በይሁዳ ሊመላለስ አይወድም ነበርና በገሊላ ይመላለስ ነበር” ይላል /ቁ.1/። ይህን የሚያደርገው ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይሁንና ፈርቶ አይደለም፡፡ የሚሰቀልበት የሚሞትበት ጊዜው ስላልደረሰ እንጂ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም! ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን ለማመልከት ለማስረዳትም አንዳንድ ጊዜ በመካከላቸው ይሄዳል፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገለል ይላል፡፡ አሁንም ተናድደውበት ነበርና ገለል አለ፤ ወደ ምድረ ይሁዳም ሊሄድ አልወደደም /St. John Chrysostom, Hom 48/፡፡  

 የአይሁድም የዳስ በዓል ቀርቦ ነበር /ቁ.2/። አይሁድ ከየአሉበት ዓለም ተሰባስበው በኢየሩሳሌም ቤተመቅደስ የሚያከብርዋቸው ሦስት ታላላቅ በዓላት አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱ ይህ የዳስ በዓል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ከየቤቶቻቸው ወጥተው በቤተ መቅደሱ ዙርያ አጠገብ፣ በከተማው ዋና ዋና አደባባይ፣ በየቤታቸው… ድንኳን ይተክላሉ፡፡ ከግብጽ ወጥተው በበረሐ በድንኳን ውስጥ ያሳለፉትን መከራና ስቃይም ያስታውሱበታል /ዘሌ.23፡29-43/፡፡

 ወንድሞቹም (ደቂቀ ዮሴፍ) ይህን ይዘው (በዓል እንደቀረበ አይተው) ጌታን እንዲህ አሉት፡- “(በምድረ ይሁዳ ያሉት) ደቀ መዛሙርትህ ደግሞ የምታደርገውን ሥራ (ተአምራትህን) እንዲያዩ  አይተውም አምላክ መሆንህን እንዲያምኑብህ ከዚህ ተነሣና ወደ ይሁዳ ሂድ፡፡ ምክንያቱም ራሱን ሊገለጥ እየፈለገ፣ ሥራው እንዲታይለት ወዶ ሳለ በስውር በድብቅ የሚሠራ የለምና። አንተም ሥራህ እንዲገለጥልህ እንዲታይልህ ትወዳለህና እነዚህን አድርገህ ራስህን ለዓለም ግለጥ፤ አምላክነትህን ለሁሉ አሳይ” አሉት /ቁ.3-4፣ ወንጌል ቅዱስ አንድምታ ገጽ 490/። እነዚህ ደቀቂ ዮሴፍ ጌታችን የሚያደርጋቸው ተአምራት ለሰው ልጆች ካለው ፍቅር የተነሣ እንደሆነ አላወቁም፤ ከማመን የዘገዩትን ሰዎች ለማቅረብ ያደረገው መሆኑን አልተረዱም፤ እንዲያው ለታይታ እንዲያው ለውዳሴ ከንቱ ያደረገው ይመሰላቸው ነበር እንጂ፤ ስለዚህ አሁን የተናገሩትን ተናገሩ፡፡ የበለጠ ይታይ ዘንድ ይህን ለገቢረ በዓል በወጣው ሕዝቡ መካከል ያደርገው ዘንድ ተናገሩት፡፡ ወንጌላዊው እንደነገረን ይህን ያሉት እነርሱ ራሳቸው ገና በጥርጥር ተይዘው ስለ ነበር ነው፡፡ የሚመጣው መሲሕ እርሱ መሆኑን ስላላመኑበት ነው፡፡ ስለዚህ በሌላ ሰው አስመስለው ይህን ተናገሩ እንጂ እናምንብህ ዘንድ ተአምራትህን አሳየን ማለታቸው ነበር /ቁ.5/፡፡

 ጌታችንስ ምን አላቸው?፡- “በገሃድ ወደ በዓል የምወጣበት ጊዜዬ፣ በይፋ መከራ መስቀል ምቀበልበት ጊዜዬ (አይሁድ ያለ ጊዘው ይገድሉት ዘንድ ይሹ ነበርና)፣ እንናንተ የምትሉት ሳይሆን እውነተኛው ክብሬ በግልጥ የሚታይበት ጊዜዬ ገና አልደረሰም፡፡ የእናንተ ጊዜ ግን የሚከለክላችሁ የለምና ለበዓለ ፋሲካውም ለበዓለ መጸለቱም ዘወትር ለመውጣት የተዘጋጀ (የተመቸ)ነው። ዓለም እናንተን ሊጠላ አይቻለውምና፡፡ እኔ ግን ሥራው ክፉ መሆኑን እመሰክርበታለሁና፤ ስለዚሁም እዘልፈዋለሁና፤ የተሰወረ ተንኰሉም እገልጥበታለሁና፤ ሌባዉን ሌባ ሲሉት አይወድምና እኔን ይጠላኛል፤ ሊገድለኝም ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ እናንተ ወደዚህ በዓል ውጡ፤ እኔ ግን በገሃድ በይፋ የምወጣበት ጊዜዬ ገና ስላልተፈጸመ አይሁድ በተናደዱበት በዚህ ጊዜ ወደዚህ በዓል ገና (ዛሬ) አልወጣም” ብሏቸው በገሊላ ቀረ /ቁ.6-9/፡፡

ከእናንተ መካከል “ጌታችን ወደዚህ በዓል ገና አልወጣም ብሏቸው ሳለ ስለምን ቀይቶ ወደ በዓሉ ሄደ” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- ጌታችን ወደ በዓሉ ጭራሽ አልሄድም ያለ አልነበረም፡፡ ገና (አሁን) አልሄድም እንጂ፤ አሁን ከእናንተ ጋር የምሄድ አይደለሁም እንጂ፡፡ በኋላ ወደ በዓሉ የወጣውም መከራ እንዲያደርሱበት፣ እንዲሰቅሉት፣ እንዲገድሉት ሳይሆን ያስተምራቸው ዘንድ ነው /St. John Chrysostom, Ibid/፡፡

  ተወዳጆች ሆይ! ከቅንዐት ተነሣስተው ጌታን ሊገድሉት ሊወግሩት ሊሰቅሉት ከሚፈልጉት ከአይሁድ ሳይሆን ከመምህራችን ከክርስቶስ ትሕትናን፣ ጥበብን፣ ትዕግሥትን የዋህነትን የምንማር እንሁን /ማቴ.11፡29/፡፡ ብዙ ሰዎች እኛን ለመጕዳት በቁጣ ነደው ይመጣሉ፤ በትሕትና እናሸንፋቸው፡፡ ብዙ ሰዎች እኛን ለመተናኰል ይመጣሉ፤ በፍቅርና በትዕግሥት እንዲሁም በጥበብ እንጠብቃቸው፡፡ ክፉው በእኛ እንዳይሰለጥን እነዚህን የከበሩ የጠቢቡ ቃላት ደጋግመን ለራሳችን እንናገራቸው፡- “እንግዲህ ትቢያና አፈር የሚሆን በሕይወትም ሳለ ሰውነቱ የሚተላ ሰው ለምን ይታበያል /ሲራክ.10፡9/፡፡ በተቈጣ ጊዜ መከራ ይመጣበታልና ቁጡና ዐመፀኛ ሰው መጽደቅ አይችልም /ሲራክ.1፡22/፡፡ በእውነቱ ከቁጣ የባሰ ክፉ ነገር የለም /ምሳሌ.11፡25/፡፡ ስለዚህ ጊዜዋን እስክታሳልፍ ድረስ ቁጣን ታገሣት፤ ኋላም ደስ ታሰኝሃለች /ሲራክ.1፡23/፡፡”
 ይህን እንድናደርግ ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን አሜን!!

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount