Friday, July 6, 2012

ሰው ከዚሁ እንጀራ ቢበላ ለዘላለም ይኖራል- የዮሐንስ ወንጌል የ30ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.6፡41-52)!


   በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
  ቅዱስ ጳውሎስ በአንድ ወቅት ስለ አንዳንድ ሰዎች ሲናገር ለፊሊጵስዮስ ክርስቲያኖች፡- “ሆዳቸው አምላካቸው ነው፤ ክብራቸው በነውራቸው ነው” ብሏቸው ነበር/ፊሊ.3፡19/፡፡ ይህ የሐዋርያው ቃል በእነዚህ የአይሁድ ሰዎች በገሃድ ሲፈጸም እናስተውለዋለን፡፡ እንዴት ቢሉ እነዚህ ሰዎች ሆዳቸው ሲሞላና ሲጠግብ ጌታችንን “ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነቢይ ነው” ይሉታል፤ ሊያነግሡትም ይሻሉ /ቁ.14-15/፡፡ የዘላለምን ሕይወት ስለሚሰጠው ሰማያዊ መና፣ ዳግም ስለማያስጠማው ይልቁንም በደስታ ስለሚንቆረቆረው አርያማዊ ውኃ ሲነግራቸው ግን ያጕረመርማሉና፡፡ ከሥጋዊው መብል ይልቅ መንፈሳዊውን መብል እንዲሹ ሲጋበዙ፣ ስለ ትንሣኤ ሕይወት ሲነገሩ፣ አልዕሉ አልባቢክሙ- ልቡናችሁን በሥጋዊው መብል ከማባከን ወደ ሰማያዊው መብል አንሡ ሲባሉ ሊደነቁና ሊገረሙ ሲገባቸው መታወክ ጀመሩ፤ “ከሰማይ የወረደ እንጀራ እኔ ነኝ” ስላለ ስለ እርሱ አንጐራጐሩ /ቁ.41/፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው ሲበሉና ሲጠግቡ “ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነቢይ ነው” ብለው ይደነቃሉ፤ ጌታችን “ከሰማይ ወርጃለሁ” ሲላቸው ግን ሊሰሙት አልወደዱም፤ ይልቁንም አንጐራጐሩበት እንጂ፡፡ እርስ በእርሳቸውምአባቱንና እናቱን የምናውቃቸው ይህ የዮሴፍ ልጅ ኢየሱስ አይደለምን? እንግዲህ ከሰማይ ወርጃለሁ እንዴት ይላል?” ተባባሉበት እንጂ /ቁ.42/። በእርግጥም በሥጋዊ ዓይን ሁሉንም የሚመለከት ሰው ከክርስቶስ አንዳች ረብሕን አያገኝም፡፡ ጌታችን እንዴት ከሰማይ እንደወረደ መመርመር፣ በዘርዐ ብእሲ የተወለደ የዮሴፍ ልጅ ነው ብሎ ማሰብ፣ እንደላው ዘንድ እንዴት ሥጋዉን ሊሰጠን ይችላል ብሎ መታወክ ሥጋዊና ደማዊ አመክንዮዎችን የሚጠይቁ ናቸውና ምንም አያገኙም፡፡ ቀዳማዊ ልደቱ በእነርሱ ዘንድ የሚመረመር አይደለም፡፡ ይህን ባለማወቃቸውም አልተወቀሱበትም፡፡ ጌታችንም “እኔስ እናንተ እንደምትሉት የዮሴፍ ልጅ አይደለሁም” አላላቸውም፡፡ የዮሴፍ ልጅ ሆኖ ሳይሆን ውስጣቸው በሌላ ነገር ስለተመላ ስለ አስደናቂው ልደቱ ቢነግራቸውም ስለማይሰሙት እንጂ፡፡ ስለ ደኃራዊ ልደቱ ካላወቁስ ስለ ቀዳማዊ ልደቱ ያውቃሉ ተብሎ እንዴት ይታሰባል? ስለዚህ ያንጐራጐሩበትን ምክንያት ትቶ በሌላ ዘዴ ያቀርባቸው ዘንድ ወደደ /Saint John Chrysostom, Homilies on St. John, Hom.46:1./፡፡

   እንዲህ ነበር ያላቸው፡- “እርስ በእርሳችሁ የምታንጐራጉሩ አትሁኑ፡፡ አለማመናችሁ ሰማያዊው ልደቴን እንዳትመለከቱ ከልክሎአችኋልና፡፡ ስለዚህም የዮሴፍ ልጅ እንደሆንኩኝ ታስባላችሁ /ቁ.43/፡፡ እኔ ግን እላችኋለሁ የላከኝ አባቴ በሀብት ስቦ በረድኤት አቅርቦ ካልሰጠኝ በእኔ ማመን የባሕርይ ልጅነቴንም ማወቅ መረዳት የሚቻለው የለም /ቁ.44፣ Saint Cyril the Great/፡፡ እንዲህ ብዬ ስነግራችሁም ነጻ ፈቃድችሁን ተጋፍቶ አባቴ በእኔ እንድታምኑ ያደርጋችኋል ማለት አይደለም፤ ይልቁንም እናንተ ለማመን ፈቃደኞች ስትሆኑ ጸጋው በእጅጉ ይረዳችኋል ማለት እንጂ፡፡ አንድ ሰው ፈቃዱን ተጋፍቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሊመጣ ይችላል፤ ከምሥዋዑ ፊት ሊቆም ይችላል፤ ሥጋዬንና ደሜንም ሊቀበል ይችላል፤ ሆኖም ግን ሐዋርያው “ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃል፤ በአፉም መስክሮ ይድናል” እንዳለ ፈቃዱን ይዞ ካልመጣ በቀር በእኔ ማመን ደግሞም መዳን የሚቻለው የለም /1ቆሮ.10፡10/፡፡ እኔ ጋር መቅረብ የሚቻለው በእግረ ሥጋ ሳይሆን በእግረ እምነት ነውና /Saint Augustine, Tractes on the Gospel of John, 26:2/፡፡

 “እናንተ እንደምታስቡት ሙሴም ቢሆን ሌላም ቢሆን አብን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ መላእክት ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉ ብዬ ስነግራችሁ እንኳ የሚያዩት ለእነርሱ በሚመጥናቸው መጠን እንጂ በባሕርይ አምላክነቱን አይደለም /ማቴ.18፡10/፡፡ እኔ ግን በባሕርይ ልጅነቴ አብን አይቼዋለሁ /ቁ.46፣ Saint John Chrysostom, ‘Divine Care’ translated by Aida Hanna, chapter 3 /፡፡


“ሁሉም ከእግዚአብሔር የተማሩ ይሆናሉ” ተብሎ እንደተጻፈ አባቴ “ዝንቱ ውእቱ ወልድዬ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሰመርኩ- ልመለክበት የወወድሁት ለተዋሕዶ የመረጥሁት ልጄ ይህ ነው” ብሎ ሲመሰክርልኝ የሰማ የተማረም ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፤ በእኔም ያምናል /ቁ.45፣ ማቴ.3፡17/፡፡ ከእናንተ መካከል “አብ አንዳንዶችን በሀብት ስቦ በረድኤት አቅርቦ በአንተ እንዲያምኑ ካደረገ ሌሎችሳ እንዲያምኑ ለምን አያደርጋቸውም?” የሚል ቢኖር፡- “እነዚያ አብ ሊስባቸው ስላልወደደ ሳይሆን በፈቃዳቸው መምጣት ስላልወደዱ ነው፤ ፈቃደኞች ሆነው በእኔ አምነው አባቴም በረድኤቱ ስቦአቸው የሚመጡትን ግን በእኔ ይኖራሉ እኔም በእነርሱ፤ በመጨረሻው ቀን አስነሣቸዋለሁ፤ መንግሥተ ሰማያትም ይወርሳሉ” ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ፡፡ ኅብስተ ሕይወት እኔ ነኝና፡፡ አባቶቻችሁ መናውን በሉ፤ ሆኖም ግን ጊዜአዊ ችግራቸውን ፈታላቸው እንጂ በምድረ በዳ ከመሞት አላዳናቸውም፤ ዘላለማዊ ደኅንነትን አልሰጣቸውም /ቁ.49-50/፡፡ እኔ ከምሰጠው ከኅብስተ ሕይወት የሚበላ ሁሉ ግን በሥጋ ቢሞት በነፍስ እንዳይሞት ፈርሶ በስብሶም እንዳይቀር ይልቁንም ትንሣኤ ዘለክብር እንዲነሣ እነግራችኋለሁ፡፡ ስለዚህ አሁንም ደግሜ እነግራችኋለሁ ከሰማይ የወረደ ኅብስተ ሕይወት እኔ ነኝ፡፡ እኔ ከምሰጠው ከዚህ ኅብስተ ሕይወት የሚበላ ሰው የተያዘበት የባርነት ቀንበር ይሰበራል፤ የኃጢአት ሰንሰለቱ ይበጣጠሳል፤ ባሕረ እሳቱን ያሻገራል፤ ወደ ዘላለማዊው ሐሴት ይነጠቃል፤ ከሲዖል እስራት ለማምለጥም ሌላ ነገር አያስፈልገውም፡፡  ክፋቱ በደግነት ይተካል፤ ጥላቻው ለፍቅር ቦታውን ይለቃል፤ አድመኝነቱ ሥፍራውን ለአንድነት ያስረክባል፤ ሌሎችም የበጐነት ዓይነቶች ነፍሱንና ሥጋዉን ለመቈጣጠር ጓዛቸውን ጠቅልለው ይመጣሉ” /ቁ.51፣ Saint Cyril the Great, Commentary on the Gospel Of John 3፡6/፡፡

  አይሁድ ግን ይህን በሰሙ ጊዜ ይህ ሰው ሥጋውን ልንበላ ይሰጠን ዘንድ እንዴት ይችላል? አንዳንድ ጉርሻስ እንኳ ይደርሰናልን? ደግሞስ የዕሩቅ ብእሲ ሥጋ ቢበሉት ደሙን ቢጠጡት ደዌ ይሆናል እንጂ ሕይወት ይሆናልን?ብለው እርስ በርሳቸው ተከራከሩ። እነርሱ የለመዱት ደመ በግዕ፣ ሥጋ በግዕ፣ ደመ ጠሊ፣ ሥጋ ጠሊ፣ ደመ ላህም፣ ሥጋ ላህም ነውና እንዲህ አሉ፡፡ ሆኖም ይህ ይሆን ዘንድ አሁን ጊዜው አይደለም፡፡ ነፍስና ሥጋን የሚቀድስ ሁለንተናንም ከኃጢአት ሁሉ የሚያነጻ ሰማያዊ መና ሰማያዊም ጽዋዕ ተሰጥቶናልና /St. Cyril Of Jerusalem, Mystagogical Lectures 4:4-6/፡፡

  አቤት! የሰይጣን የማታላያ መንገዱ እንዴት ብዙ ነው? አስቀድሞ የአይሁድን ልብ እንዳሳወረ ዛሬም ሰዎች ራሳቸው ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ክቡር ደሙ መቅረብ እንደሚገባቸው ፈጽመው እንዳያስቡት ያደርጋቸዋል፡፡ በክፋት ላይ ክፋት እያሠራ ከጸጋው እንዲርቁ ተራና መናኛ ምክንያትን ያቀርብላቸዋል፡፡ በቲሃ ወይን ጠጃቸው ከአፋቸው እንዳልተወገደ ሰካራሞች  ለራሳቸው የሚጠቅማቸው ነገር እንዲመለከቱ ዕድል አይሰጣቸውምና በክፋት ላይ ክፋት እየጨመሩ ይሄዳሉ /ኢዩ.1፡5/፡፡ እንግዲያውስ ሰይጣን በእኛ ላይ የጫነውን ቀንበር ሰብረን የታሰርንበትንም ማሰርያ በጥሰን እግዚአብሔርን በፍርሐትና በመንቀጥቀጥ እናገልግለው፡፡ መጽሐፍ እንደሚል ለእግዚአብሔር በፍርሐት እንገዛ፤ በረዓድም ደስ ይበለን /መዝ.2፡11/፡፡ ራሳችንን በመቈጣጠር ከሥጋ ፈቃድና ፍላጐት በላይ ሆነን የተፈጠርን መሆናችንን እናሳይ፡፡ ሰማያዊውንና መለኰታዊውን ጸጋ እንቅረበው፡፡ ወደ ክርስቶስ ሥጋና ደም በድፍረት ሳይሆን በእምነትና በፍርሐት እንቅረብ፡፡ የሰይጣንን ማታለል የምንመለከትበት ትክክለኛው መንገድ ይኼው ብቻ ነውና፡፡ “ከመለኰት ባሕርይ ተካፋዮች” ከሆንን ወደማይጠፋና የማይሞት የዘላለም ሕይወት እንሸጋገራለን /2ጴጥ.1፡4፣ ቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ በዲ/ን ታደለ ፈንታው ገጽ 148/፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!




No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount