Thursday, April 30, 2015

ስለ ጌጠኛ ልብስ

በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ 22 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ዕርቃናችንን የምንሸፍንበት ልብስ ብቻ ልንለብስ ይገባናል፡፡ ብዙ ወርቅን ብናደርግ ምንድነው ትርጉሙ? ብዙ ወርቅን ማድረግ በተውኔት ቤት ነው፤ ተዋንያን ብዙ ተመልካችን ለማግኘት ያደርጉታልና፡፡ ጌጠኛ ልብስ መልበስ የአመንዝራ ሴቶች ግብር ነው፤ ብዙ ወንዶች ይመለከቷቸው ዘንድ ይኽን ያደርጋሉና፡፡ እነዚኽን ማድረግ ልታይ ልታይ ለሚሉ ሰዎች ነው፡፡ እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት የምትሻ ሴት ግን ይኽን ጌጥ ማድረግ አትፈልግም፡፡ ራሷን የምታስጌጠው በሌላ መንገድ ነው፡፡ እናንተም ይኽን ጌጥ ማድረግ የምትፈልጉ ከኾነ ማድረግ ትችላላችኁ፡፡ ተውኔት ቤትን የምትሹ ከኾነም ወርቀ ዘቦአችኁን የምታደርጉበት ሌላ ተውኔት ቤት አለላችኁ፡፡ ያ ተውኔት ቤትስ ምንድነው? መንግሥተ ሰማያት ነው፡፡ ተመልካቾቹ ቅዱሳን መላእክት ናቸው፡፡ ይኽን የምናገረው በገዳም ለሚኖሩት መኖኮሳይያት ብቻ አይደለም፤ በማዕከለ ዓለም ለሚኖሩትም ኹሉ ጭምር እንጂ፡፡ በክርስቶስ ክርስቲያን በወልድ ውሉድ የተባለ ኹሉ የራሱ ተውኔት ቤት አለው፡፡ ስለዚኽ ተመልካቾቻችንን ደስ ለማሰኘት ራሳችንን ደኅና አድርገን እናጊጥ ብዬ እማልዳችኋለኁ፡፡ ለመድረኩ የሚመጥን ልብስን እንልበስ፡፡ እስኪ ንገሩኝ! አንዲት ሴሰኛ ሴት ተውኔት ለመሥራት ብላ ብዙ ወርቋን አወላልቃ፣ ቄንጠኛ መጎናጸፍያዋን ጥላ፣ በሳቅ በስላቅ ሳይኾን ቁም ነገርን ይዛ፣ ተርታ ልብስን ለብሳ ወደ መድረኩ ብትወጣና ሃይማኖታዊ ንግግርን ብትናገር፣ ስለ ንጽሕና ስለ ቅድስና ብትናገር፣ ሌላ ክፉ ንግግርም ባትጨምር በተውኔት ቤቱ የሞላው ሰው አይነሣምን? ተመልካቹ ኹሉ የሚበተን አይደለምን? ሰይጣን የሰበሰበው ተመልካቹ የማይፈልገውን ነገር ይዛ ስለ መጣች ኹሉም የሚሳለቅባትና እንደ ትልቅ አጀንዳ የሚወራላት አይደለምን? አንተም በብዙ ወርቅ፣ በጌጠኛ ልብስ ተሸላልመኽ ወደ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ቅዱሳን መላእክት አስወጥተው ይሰዱኻል፡፡ ምክንያቱም በመንግሥተ ሰማያት የሚያስፈልገው ልብስ እንደዚኽ ዓይነት አይደለም፤ ሌላ ነው እንጂ፡፡ “ርሱስ ምን ዓይነት ነው?” ትለኝ እንደኾነም “ነፍስን በትሩፋት ማስጌጥ ነው” ብዬ እመልስልኻለኁ፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት፡- “ልብሷ የወርቅ መጐናጸፍያ ነው” ያለውም ይኽንኑ ነው እንጂ በዚኽ ምድር የምንለብሰው ልብሳችንን ፀዓዳና አንጸባራቂ ስለ መኾን አይደለም /መዝ.45፡13/፡፡ ምክንያቱም “ለሐሴቦን ንጉሥ ልጅ ኹሉ ክብሯ ነው” እንዳለ በዚያ (በመንግሥተ ሰማያት) መራሔ ተውኔቷ ርሷ ናት፡፡ እኅቴ ሆይ! ራስሽን መሸላለም ብትፈልጊ እንዲኽ አጊጪ፡፡ ከዚያም ከምረረ ገሃነም ትድኛለሽ፡፡ ባልሽንም ከማዘን ከመቆርቆር ትታደጊዋለሽ፡፡

Tuesday, April 28, 2015

የጉባኤ ጥሪ ከዓምደ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት

“ተዋሕዶ ሃይማኖታችን፣ ቤተ ክርስቲያን እናታችን” በማለታቸው በዓለማቀፉ አሸባሪ ቡድን በአይሲስ የተገደሉት ኢትዮጵያውያን ሰማዕታትን ለማሰብ የመንበረ መንግሥት (ግቢ) ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ዓምደ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት ሚያዝያ 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ልዩ መንፈሳዊ ጉባኤ አዘጋጅቷል፡፡ በዕለቱ “ሰማዕትነት በዘመናችን” በሚል ዐቢይ ርእስ የምክክር ጉባኤ የሚደረግ ሲኾን ሚያዝያ 20፣ 21፣ እና 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሦስት ተከታታይ ቀናት ከቀኑ 12፡00 ሰዓት ዠምሮ የጸሎት መርሐ ግብር ይካሔዳል፡፡

የመስቀሉ ሕዝቦች

      (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ 20 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡-በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 በቅርቡ አይሲስ  የተባለው “ሃይማኖታዊ” ድርጅት “ክርስቲያን መግደል ገነት ያስገባል ፤ አላህ ደማቸውን እያየ ደስ ይለዋል” በሚል እንኳን መንፈሳዊነት ሰብአዊነት በጎደለው ፍፁም ሰይጣናዊ ትምህርት መነሻ በማድረግ ምንም የማያውቁትን ምስኪኖች በጭካኔ ግማሹን በተማሩት ትምህርት እንደበግ እያረዱ ግማሹን ደግሞ በጥይት እያርከፈከፉ ፈጅተዋቸዋል፡፡ በዚህም የኦርቶዶክሳውያን ልብ ፍፁም አዝኗል፤ አልቅሷል፡፡
ይሁን እንጂ ‹‹ መሳ ፲፬፡ ፰ - ፲፬ ከበላተኛው መብልን የሚያወጣ ››ጌታ ከእነዚህ አረመኔዎች አንድ አስደናቂ ቃል አሰምቶናል፡፡ ይኸውም እነዚህ አረመኔዎች ምስኪኖቹን ኦርቶዶክሳውያን ከማረዳቸው በፊት ሁሉንም በወል የጠሩበት ስም ‹‹ የመስቀሉ ሕዝቦች ›› የሚል ነው፡፡ መጽሐፍ  በ‹‹ዮሐ ፲፩ ፤ ፵፱ በዚያችም አመት የካህናት አለቃ የነበረው ስሙ ቀያፋ የተባለው ከእነርሱ አንዱ እንዲህ አላቸው ‹ እናንተስ ምንም አታውቁም ፤ ምንም አትመክሩም ሕዝቡ ሁሉ ከሚጠፋ  ስለ ሕዝቡ አንድ ሰው ቢሞት ይሻለናልና ›፡፡ ይህንም ከልቡ የተናገረ አይደለም ፤ ነገር ግን በዚያች አመት የካህናት አለቃ ነበርና ጌታችን ኢየሱስ ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ ስላለው ይህን ትንቢት ተናገረ፡፡››  እንደሚል ቀያፋን ክርስቶስ ለሰው ዘር በሙሉ በፈቃዱ ይሞት ዘንድ እንዳለው ትንቢት ይናገር ዘንድ ያደረገ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ፤ ዛሬም እነዚህን አረመኔዎች አፋቸውን ከፍቶ ፊታቸውን ጸፍቶ ስለ ኦርቶዶክሳውያን ያስመሰከራቸው ቃል እንጂ ወደው አስበው የተናገሩት አይደለም፡፡ ለዚህም አንዳንድ ማሳያዎችን ላቅርብ፡፡

Saturday, April 25, 2015

ሰማዕታት

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ 17 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
        ሰማዕት የሚለው ቃል ስርወ ቃሉ “ሰምዐ” የሚል ሲኾን ይኸውም ሰማ፣ አደመጠ፣ አስተዋለ፣ ተቀበለ፣ መሰከረ፣ ምስክር ኾነ፣ ያየውን የሰማውን ተናገረ፤ አየኹ ሰማኹ አለ ማለት ነው፡፡ በመኾኑም ሰማዕት ማለት የሚመሰክሩ፣ ሃይማኖታቸውን መስክረው በሰማዕትነት የሚሞቱ ማለት ነው፡፡ ለአንድ ሰማዒ ሲኾን ሲበዛ ሰማዕት ይኾናል፡፡
በቤተ ክርስቲያን ታሪክ የሰማዕታት መዠመሪያ የሚባለው አቤል ነው፡፡ በአክአብና በኤልዛቤል ትእዛዝ በድንጋይ ተወግሮ በግፍ የተገደለው ናቡቴ፣ በይሁዳ ንጉሥ በምናሴ ትእዛዝ በእግሮቹና በራሱ መካከል በመጋዝ ተሰንጥቆ የሞተው ነቢዩ ኢሳይያስ፣ እንዲኹም በአይሁድ በድንጋይ ተወግሮ የተሠዋው ነቢዩ ኤርምያስም ተጠቃሾች ናቸው፡፡
በዘመነ ሐዲስም ከሕፃናተ ቤተ ልሔም የዠመረው በእነ ካህኑ ዘካርያስ፣ መጥምቁ ዮሐንስ፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ጳውሎስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ቅዱስ መርቆሬዎስ፣ ቅዱስ ቂርቆስ፣ በአጠቃላይ በዲዮቅልጥያኖስና መክስምያኖስ የተጨፈጨፉት የሦስተኛውና የአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሰማዕታት በዋናነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
በኢትዮጵያም ሰማዕትነትና ክርስትና የአንድ ሳንቲም ኹለት ገጽታዎች ናቸው፡፡ ዮዲት ጉዲት፣ ግራኝ አሕመድ፣ ሱስንዮስ፣ ፋሺስት ጣልያን፣ ደርግ፣ እንዲኹም በቅርቡ በአርሲ በምዕራብ ሐረርጌ በጅማ አጋሮ በአክራሪ ሙስሊሞች የተፈጸሙት ለዚኽ ማሳያዎች ናቸው፡፡
ከዚኽ በመቀጠል ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “The Cult of the Saints - ፍኖተ ቅዱሳን” በተሰኘ መጽሐፍ በጊዜው ለነበሩ ምእመናን ስለ ተለያዩ ሰማዕታት ያስተማራቸውን ትምህርት ከአኹኑ ኢትዮጵያውያን ሰማዕታት ጋር እያገናዘብኩ የተረጐምኩትን በአጭሩ አቅርቤላችኋለኁ፡፡ መልካም ንባብ፡፡

Thursday, April 23, 2015

ሰው ሲሞትብን ምን እናድርግ?

በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ 15 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ልጆቼ! ክርስቲያን ሲያርፍ አግባብ የሌለው ለቅሶ አይለቀስም፡፡ ታላቅ የኾነ ሥነ ሥርዓት እየተካሔደ ሳለ ለቅሶ አይለቀስም፡፡ እማልዳችኋለሁ! እስኪ ልጠይቃችሁና እናንተም መልሱልኝ! ኹላችንም በአንድ ቦታ ተሰብሰበን ሳለ የሀገራችን ንጉሥ ለአንዳችን የጥሪ ወረቀት ልከው ለእራት ግብዣ ጠሩን እንበል፡፡ ከእኛ መካከል ወደ ንጉሡ ተጠርቶ ስለ ሔደው ሰው የሚያለቅስ ማን ነው?

Wednesday, April 15, 2015

መንፈሳዊ ሕይወት ከትንሣኤ እስከ ጰራቅሊጦስ

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ 8 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
(ይኽ ጽሑፍ ከዚኽ በፊት ተለጥፎ የነበረ ነው)
        በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ከትንሣኤ እስከ ጰራቅሊጦስ እሑድ ባለው ወራት ረቡዕንና ዓርብን ጨምሮ አይጦምም፤ የቀኖና ስግደትም አይሰገድም፡፡ ይኽም ሠለስቱ ምዕት በ325 ዓ.ም. በጉባኤ ኒቅያ ሲሰበሰቡ በሀያኛው ቀኖኗቸው የወሰኑት ቀኖና ነው /ሃይ.አበ.20፡26፣ The Oxford Dictionary of the Christian Church, pp 1250, 1738/፡፡ ይኽን ቀኖና ሲወስኑም ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ይኽ ወራት ከትንሣኤ ዘጉባኤ በኋላ ያለውን ሕይወታችን የሚያሳይ ስለኾነ ነው እንጂ፡፡ ከትንሣኤ ዘጉባኤ በኋላ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ለማስገዛት ተብሎ የሚደረግ ጦምም ኾነ ስግደት የለም፡፡ ሰውነታችን ሙሉ በሙሉ በዲያብሎስ ከመፈተን፣ ከእግዚአብሔር ውጪ የኾነ ሌላ ሐሳብን ከማሰብ ነጻ የሚወጣበት ወራት ነው፡፡ በዚያ ሰዓት ፈቃዳችን ከፈቃደ እግዚአብሔር ጋር የተስማማ ነው፡፡ ሥጋ ሙሉ ለሙሉ ከድካሙ ነጻ ስለሚኾን እግዚአብሔርን ለማመስገን ትጉኅ ነው፡፡ እንደ አኹኑ እንቅልፍ እንቅልፍ አይለውም፤ ዘወትር የቅዱሳን መላእክትን ምግብ ለመብላት ማለትም ለማመስገን የተዘጋጀ ነው እንጂ፡፡

Monday, April 13, 2015

ትምህርተ ሃይማኖት (ክፍል ዘጠኝ)

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ 6 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
        ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን - በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን
        አሰሮ ለሰይጣን - አግዐዞ ለአዳም
        ሰላም - እምእዜሰ
        ኮነ - ፍሰሐ ወሰላም
        ውድ የመቅረዝ አንባብያን! እንዴት አላችኁ? የትምህርተ ሃይማኖት ትምህርቱን እየተከታተላችኁ እንደኾነ ጽኑ እምነቴ ነው፡፡ እስከ አኹን ድረስ የትምህርተ ሃይማኖት መግቢያ፣ የሃይማኖት አዠማመርና እድገት፣ ከኹሉም በፊት አንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ማወቅ ያለበት ብለን ነገረ ቤተ ክርስቲያን፣ ቅዱስ ትውፊት፣ ኦርቶዶክሳዊ የመጽሐፍ ቅዱስ አረዳድ፣ ስለ ዶግማና ቀኖና፤ ስለ እግዚአብሔር መኖርና ስለ ባሕርዩ ጠባያት እንዲኹም ስሙ ማን እንደኾነ ተማምረናል፡፡ ዛሬም ሥነ ፍጥረት ብለን እንቀጥላለን፡፡ እግዚአብሔር ማስተዋልን ያድለን፡፡ አሜን!!!

Saturday, April 11, 2015

መቅረዝ ዘተዋሕዶ: በዓለ ትንሣኤ

መቅረዝ ዘተዋሕዶ: በዓለ ትንሣኤ: በገብረ እግዚአብሔር (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሚያዝያ ፲፩ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! የዚኽ ትምህርት መሠረታዊ ዓላማ ክርስቲያኖች ክርስቶስን መስለው ...

Tuesday, April 7, 2015

በአስቆሮቱ ይሁዳ ዙርያ የሚነሡ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መጋቢት 30 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
        ጌታችንን አሳልፎ የሰጠው ከዐሥራ ኹለቱ ሐዋርያት የነበረው የአስቆሮቱ ይሁዳ ነው፡፡ አስቆሮት በይሁዳ አውራጃ የሚገኝ ቂርያትሐጾር የሚባል መንደር ነው /ኢያሱ.15፡25/፡፡ የሐዋርያት ገንዘብ ያዥ ኾኖ ሳለ ለራሱ ገንዘብ ይሰርቅ ነበር፡፡ በኋላም ስለ ገንዘብ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ተስማምቷል፡፡ ብዙ ሰዎች በይሁዳ ዙርያ የተለያዩ ጥያቄዎችን ያነሣሉና ለዚኽ መልስ ይኾነን ዘንድ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የማቴዎስ ወንጌልን በተረጐመበት 81ኛው ድርሳኑ ላይ የተናገረውን ወደ አማርኛ መልሼ አቅርቤላችኋለኁ፡፡ መልካም ንባብ!!!

Thursday, April 2, 2015

በፌስ ቡክ የምጽፈውና የእኔ ማንነት አይገናኝም፡፡ ምን ላድርግ?



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐሙስ መጋቢት 24 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ውድ መቅረዛውያን እንዴት አላችኁ? ዛሬም ከአንባብያን ከተላኩልኝ ጥያቄዎች ለሦስተኛው ጥያቄ የተሰጠውን ምላሽ አቀርብላችኋለኁ፡፡ መልሱን የሚሰጡን በምሥራቀ ፀሐይ ቀበና መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን ሰባኬ ወንጌል እንዲኹም በታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳም የመጻሕፍተ ሐዲሳት የ5ኛ ዓመት ደቀ መዝሙርና የዘንድሮ ተመራቂ የኾኑት ቀሲስ ፋሲል ታደሰ ናቸው፡፡ የልድያን ልቡና የከፈተ አምላክ የእኛንም እዝነ ልቡናችን ይክፈትልን፡፡ አሜን!!!

FeedBurner FeedCount