Wednesday, May 30, 2012

አብ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድ ደግሞ ይህን እንዲሁ ያደርጋል- የዮሐንስ ወንጌል የ25ኛ ሳምንት ጥናት (ዮሐ.5፡18-28)=+=


     ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እነርሱ መዳን ብሎ ወደ ቤታቸው ቢመጣም፣ በኃይልና በሥልጣን የሚያደርገውን ሁሉ ሲያደርግ ቢመለከቱትም መጻሕፍትን ከመመርመር ይልቅ፣ ትንቢተ ነብያትን ከማገናዘብ ይልቅ አይሁድ የራሳቸውን ወግ በመጥቀስ ሊገድሉት ይፈልጉ ነበር፡፡ የሚናገረውን እንኳን ባያምኑ የሚያደርገውን አይተው ወደ እርሱ እንዲመጡ በተገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ይባስኑ ውስጣቸው በቅናት ይቆስል ነበር፡፡ ስለዚህም “ሰንበትን ስለሻረ ብቻ ሳይሆን ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር ስለሚያስተካክል ይህ ሰው ከእግዚአብሔር አይደለም” ለማለት ደፈሩ /ቁ.18/፡፡ ጌታችን ግን አንዳንድ ልበ ስሑታን እንደሚሉት “ስለምን ልትገደሉኝ ትፈልጋላችሁ? እኔ ከአብ ጋር የተካከልኩ አይደለሁም” ወይም “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል እኔም አገለግላለሁ” ሳይሆን “አባቴ እስከ ዛሬ (ቅዳሜ ቅዳሜ) ይሠራል (አንዳንድ ድውይ ይፈውሳል) እኔም እንዲሁ እሠራለሁ (መጻጉዕን ፈወስኩ)” ይላቸዋል /ቁ.17/፡፡ ወንጌላዊው እዚህ ጋር የአይሁዳውያኑ አባባል ትክክል ስለነበረ በሌላ ቦታ /ዮሐ.2፡19/ እንደሚያደርገው ማስተካከያ አላደረገበትም፤ ከዚህ በፊት እንዳደረገውም “አይሁድ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር እንዳስተካከለ ቢያስቡም ክርስቶስ ግን እንዲህ ማለቱ ነበር” አይልም /Saint John Chrysostom Homilies on St. John, Hom 38./፡፡

   ከዚህ በኋላ ስለ ሰው ልጆች መዳን አብዝቶ የሚሻ ጌታችን እንዲህ ይላቸዋል፡- “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም” /ቁ.19/፡፡ ምን ማለት ይሆን? እውነት “ነፍሴን ላኖራትም ላነሣትም ሥልጣን አለኝ” ያለው ጌታ ምንም ሊያደርግ አይችልምን? /ዮሐ.10፡18/፡፡ ወንድሞቼ ይህን በጥንቃቄ ልናስተውለው ይገባል፡፡ ይህ መለኰታዊ ቃል አንዳንዶች እንደሚያስቡት ሳይሆን እንዲህ ማለቱ ነው፡- “እኔ ከራሴ ብቻ አንቅቼ ምንም ምን ሥራ አልሠራም፤ ከአብ በሕልውና ያየሁትን በህልውና ያገኘሁትም እሠራለሁ እንጂ፡፡ የአብ ፈቃድ የእኔ ፈቃድ ናት፤ የአብና የእኔ ፈቃድ እርስ በእርሷ የምትለያይ አይደለችም፡፡ እስከ ዛሬ አብ የወደደውን ሲያደርግ እንደነበረ እኔም እንዲሁ (በተመሳሳይ ሥልጣን በተመሳሳይ ዕሪና) የወደድኩትን አደርጋለሁ፡፡ አብ ይፈውስ እንደነበረ እኔም እፈውሳለሁ፡፡ ስለዚህ አብ አባቴ ነው ስላልኳችሁ አትደነቁ፤ ከአባቴ ጋር የተካከልኩ ነኝ ስላልኳችሁ አትበሳጩ፡፡ እናንተን ለማዳን ብዬ ምንም ከአባቴ ጋር ያለኝን መተካከል እንደመቀማት ሳልቆጥረው የእናንተ የባርያቼን መልክ ብይዝም አብ የሚያደርገውን ሁሉ እኔ ደግሞ ይህን እንዲሁ አደርጋለሁና /ፊል.2፡6/፤ የአብ የሆነ ሁሉ የእኔ ነውና፤ የእኔም የሆነ ሁሉ የአብ ነውና /ዮሐ.17፡10/፡፡ የሆነው ሁሉ በእኔ የሆነው አብ መፍጠር የማይችል ሆኖ ሳይሆን በሥላሴ ዘንድ የፈቃድ ልዩነት ስለሌለ ነው” /ዮሐ.1፡3 Saint AmbroseOf the Holy Spirit Book 2:8:69/። በእርግጥም ክርስቶስ አልዓዛርን ከሞት ሲያስነሣው አብ ምንም አላደረገም አይባልም /ዮሐ.11፡42/፤ ክርስቶስ የዓይነ ሥውሩን ብርሃን ሲመልስለት መንፈስ ቅዱስ ምንም አላደረገም አይባልም /ዮሐ.9፡3/፡፡ የሥላሴ ሥራ በአንድነት በአንድ ፈቃድ የሚደረግ እንጂ በተናጠል የሚደረግ አይደለምና /Saint Augustine. Sermon on N.T. Lessons, 76:9/፡፡

Sunday, May 27, 2012

ታላቅ መሆንን ስትፈልጉ ታላቅ መሆንን አትፈልጉ ከዚያም ታላቅ ትሆናላችሁ


ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ሲያሰተምር እንዲህ አለ፡- “ማንም ከእናንተ ታላቅ መሆን የሚወድ የእናንተ አገልጋይ ይሁን… ማንም ፊተኛ ሊሆን የሚወድ የእናንተ ባርያ ይሁን… ታላቅ መሆንን ማሰብ የክፉዎች ሐሳብ ነው… የመጀመርያነትን ስፍራ መፈለግ የክፋት ሁሉ ምንጭ ነው… ታላቅነትን መፈለግ ታናሽነት ነው፡፡
   ስለዚህ ይህን ልቡና ከእናንተ ገርዛችሁ ጣሉት… በእናንተ በክርስቲያኖች ዘንድ እንዲህ አይደለም… በአሕዛብ ዘንድ የመጀመርያነትን ስፍራ የሚይዙ በሌሎች ዘንድ አለቆች እንዲሆኑ ነው… በእኔ ዘንድ ግን የመጨረሻውን ስፍራ የሚይዝ እርሱ የመጀመርያ ነው፡፡
   ይህን ከእኔ መማር ትችላላችሁ… እኔ ምንም የነገሥታት ንጉሥ የአለቆችም አለቃ ብሆንም በፈቃዴ የባርያዎቼን የእናንተን መልክ እይዝ ዘንድ አልተጠየፍኩም… በሰዎች ዘንድ የተገፋሁ ሆንኩ… ተተፋብኝ… ተገረፍኩኝ… ይህም ሳይበቃኝ በመስቀል ሞት ሞትኩኝ፡፡ ነገር ግን ላገለግል ስለ ብዙዎችም ነፍሴን ቤዛ ልሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉኝ አልመጣሁም፡፡ ቤዛነቴም ለወዳጆቼ ብቻ ሳይሆን ለሚጠሉኝም ለሚወግሩኝም ለሚያሰቃዩኝም ጭምር ነው፡፡ የእናንተ አገልጋይነት ግን ለእናንተ ለራሳችሁ እንጂ ለሌሎች ቤዛነት የሚሆን አይደለም፡፡
  እንዲህ አድርጌ ስነግራችሁ ክብራችሁ ዝቅ ዝቅ ያለ መስሎ አይታያችሁ… ምንም ያህል ዝቅ ዝቅ ብትሉም እኔ የተዋረድኩትን ያህል አትዋረዱም… እኔ ይኼን ያህል ከመጨረሻው የክብር ጠርዝ ወደ መጨረሻው የውርደት ጠርዝ ብወርድም ለብዙዎች መነሣት ሆንኩኝ… ክብሬ ከመቃብር በላይ ሆነ… ክብሬ በዓለም ላይ ከአጥብያ ኮከብ በላይ ደመቀ፡፡ ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ከመወለዴ በፊት መታወቄ በመላእክት ዘንድ ብቻ ነበር… አሁን ሰው ከሆንኩኝ በኋላ ግን ክብሬ በመላእክት ብቻ ሳይሆን በሰው ዘንድም የታወቀ ነው፡፡

አንድ ፕሮቴስታንት ለጠየቀኝ የተለያዩ ጥያቄዎች በጽሑፍ የሰጠሁት ምላሽ

        በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!  

   1. “በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ፥ ጠላቶቹም አፈር ይልሳሉ። የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የዓረብና የሳባ ነገሥታት እጅ መንሻን ያቀርባሉ።”  እና “የግመሎች ብዛት፥ የምድያምና የጌፌር ግመሎች፥ ይሸፍኑሻል፤ ሁሉ ከሳባ ይመጣሉ፥ ወርቅንና ዕጣንን ያመጣሉ የእግዚአብሔርንም ምስጋና ያወራሉ።” ተብሎ በነብያቱ የተነገረውን ትንቢት በቀጥታ “ወደ ቤትም ገብተው ሕፃኑን ከእናቱ ከማርያም ጋር አዩት፥ ወድቀውም ሰገዱለት፥ ሣጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን ከርቤም አቀረቡለት።” ተብሎ ሲፈጸም ስለምንመለከተው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ. ጌታ ሲወለድ በቤተልሔም ተመሠረተች ቢባል ያስኬዳል /መዝ.71፡9-10፣ ኢሳ.60፡6፣ ማቴ.2፡1-11/፡፡ በኋላ ደግሞ የሐዋርያት ሥራ ጸሐፊ እንደሚነግረን፡- “የጌታም መልአክ ፊልጶስን። ተነሥተህ በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ ወደሚያወርደው ምድረ በዳ ወደ ሆነ መንገድ ሂድ አለው።ተነሥቶም ሄደ። እነሆም፥ ህንደኬ የተባለች የኢትዮጵያ ንግሥት አዛዥና ጃንደረባ የነበረ በገንዘብዋም ሁሉ የሠለጠነ አንድ የኢትዮጵያ ሰው ሊሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር፤ሲመለስም በሰረገላ ተቀምጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ያነብ ነበር። መንፈስም ፊልጶስን። ወደዚህ ሰረገላ ቅረብና ተገናኝ አለው። ፊልጶስም ሮጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ሲያነብ ሰማና። በውኑ የምታነበውን ታስተውለዋለህን? አለው። እርሱም። የሚመራኝ ሳይኖር ይህ እንዴት ይቻለኛል? አለው። ወጥቶም ከእርሱ ጋር ይቀመጥ ዘንድ ፊልጶስን ለመነው።ያነበውም የነበረ የመጽሐፉ ክፍል ይህ ነበረ፤ እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፥ የበግ ጠቦትም በሸላቹ ፊት ዝም እንደሚል፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። በውርደቱ ፍርዱ ተወገደ፤ ሕይወቱ ከምድር ተወግዳለችና ትውልዱንስ ማን ይናገራል?  ጃንደረባውም ለፊልጶስ መልሶ። እባክህ፥ ነቢዩ ይህን ስለ ማን ይናገራል? ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ? አለው። ፊልጶስም አፉን ከፈተ፥ ከዚህም መጽሐፍ ጀምሮ ስለ ኢየሱስ ወንጌልን ሰበከለት። በመንገድም ሲሄዱ ወደ ውኃ ደረሱ፤ ጃንደረባውም። እነሆ ውኃ፤ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምንድር ነው? አለው። ፊልጶስም። በፍጹም ልብህ ብታምን፥ ተፈቅዶአል አለው። መልሶም። ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ አምናለሁ አለ። ሰረገላውም ይቆም ዘንድ አዘዘ፥ ፊልጶስና ጃንደረባው ሁለቱም ወደ ውኃ ወረዱ፥ አጠመቀውም። ከውኃውም ከወጡ በኋላ የጌታ መንፈስ ፊልጶስን ነጠቀው፤ ጃንደረባውም ሁለተኛ አላየውም፥ ደስ ብሎት መንገዱን ይሄድ ነበርና።” ይለናል /ሐዋ.8፡26-39/፡፡ ይህም የሆነው በ34 ዓ.ም. ነው፡፡ በይፋ በጳጳስ መመራት የጀመረችው ግን በ330 ዓ.ም. በአባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን አማካኝነት ነው፡፡
  • “ኦርቶዶክስ” የሚለው ቃል “ኦርቶዶክስያ” ከሚለው የግሪክ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ቀጥተኛ (እምነት) ማለት ነው፡፡ የምስራቅና የኦሬንታል አብያተ ክርስቲያናትም ይጠሩበታል፡፡
  • “ተዋሕዶ” የሚለው ቃል በግሪኩ “Miaphysis” የሚለውን ቃል የሚተካ የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ክርስቶስ ሰው የሆነ አምላክ መሆኑን /ዮሐ.1፡1፣14/፣ መለኰትና ትስብእትም ያለ መለያየት፣ ያለ መቀላቀል፣ ያለ መለያየት ስለ ተዋሐዱ አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ ፈቃድ፣ አንድ ግብር መሆኑን የሚገልጽ ነው፡፡
     

Wednesday, May 23, 2012

ከሁሉ በታች ቁጫጭ ስንሆን ከሁሉም በላይ አደረገን=+=



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ጸሐፊ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ እንደሚነግረን አሁን ካሣው ተከፍሏል፤ አናቅጸ ሲዖል ተሰባብሯል፣ የሰው ልጅም እንደ ድሮ በዕዳ በቁራኝነት ከመያዝ ነጻ ወጥቷል፤ ጌታችንም ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷል፡፡ እንዴት ያለ ፍቅር ነው?
 ተነሥቶም ለአርባ ቀናት ያህል ደቀመዛሙርቱን ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ምሥጢር ሲነግራቸውና ሲያስረዳቸው ቆየ /ሐዋ.1፡3/፤ [ይህ ትምህርት ሊቃውንቱ እንደሚነግሩን መጽሐፈ ኪዳን ይባላል!] “ልባችሁ አይታወክ በእግዚአብሔር እመኑ በእኔም ደግሞ እመኑ፡፡ በአባቴ ቤት ብዙ መኖርያ አለ፡፡ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበረ፡፡ ሥፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና” እያለ ከዚህ በፊት የነገራቸውን እየደገመ የደቀመዛሙርቱን ልብ ሰማያዊውን ሕይወት እንዲናፍቅ ያደርገው ነበረ /ዮሐ.14፡1/፡፡ ሆኖም ግን እየተገለጠላቸው እንጂ ከዚህ በፊት ሲያደርገው እንደነበረ ቀንና ሌሊት ሁሉ ከእነርሱ ጋር በመዋልና በማደር አልነበረም፡፡ አሁን ስለ እኛ ብሎ ዝቅ ያለበት ያ ደካማ ማንነቱ የለምና፤ አሁን ያ የለበሠው ባሕርያችን በአዲስ መንፈሳዊ አካል ተነሥቷልና፡፡ 

FeedBurner FeedCount