Showing posts with label ጥያቄና መልስ. Show all posts
Showing posts with label ጥያቄና መልስ. Show all posts

Wednesday, July 11, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል አራት!


      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ውድ ክርስቲያኖች! የእግዚአብሔር ፍጹም ሰላም ይብዛላችሁ! አሜን!
በክፍል ሦስት ትምህርታችን ወደ ስድስት የሚሆኑ ነጥቦችን አይተን ነበር፡፡ ለዛሬም ቸሩ አምላካችን በፈቀደልን መጠን ካቆምንበት እንቀጥላለን፡፡
1. መሥዋዕትን አንዴ (አንድ ጊዜ) ያቀረበ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ለኃጢአት ሥርየት የሚያቀርቡት መሥዋዕት ፍጹም ድኅነትን ስለማይሰጥ ዕለት ዕለት ይሠዉ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን አንድ ቀን ስለ ዓለም ሁሉ መዳን በቀራንዮ ላይ መሥዋዕት አድርጎ ባቀረበ ጊዜ የዓለምን ኃጢአት ስላስወገደ በእርሱ ያመነ ሁሉ ተረፈ ኃጢአት (የማይደመሰስ ኃጢአት) ስለማይኖርበት በየጊዜው ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ አያስፈልገውም፡፡ ዓለም ሁሉ በእርሱ ካመነ በዕለተ ዐርቡ መሥዋዕት ይድናል እንጂ ሌላ ተጨማሪ መሥዋዕት አይቀርብለትም፡፡ የኃጢአተኛ ተለዋጭ ሆኖ የቀረበው የመሥዋዕቱ በግ ክርስቶስ አንድ ነውና /ዕብ.7፡27-28/፡፡ ስለዚህ አንድ ጊዜ አምነን ተጠምቀን የክርስቶስ ማደርያ ከሆንን በኋላ ክፉ ሐሳብ ወደ ራሳችን ሰብስበን ወይም ደግሞ ሰው አገብሮን ተጋፍቶን በገቢር ብንበድል (ሃይማኖታችንን  ክደን ቆይተን ብንመለስ እንኳን) ዳግመኛ ንስሐ ገብተን እንመለሳለን እንጂ ከእንግዲህ ወዲህ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ ሁለተኛ ጥምቀት ሁለተኛ መሥዋዕት አይቀርብልንም፤ ወልደ እግዚአብሔርንም ዳግመኛ ተሰቀልልን መከራ ተቀበልልን የለምንለው አይደለም /ዕብ.10፡26/፡፡
2. በአብ ቀኝ የተቀመጠ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ወደ ምድራዊቱ ቅድስት ሥፍራ በዓመት አንድ ጊዜ በብዙ ፍርሐትና ረዐድ ይገቡ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እንዲህ አልገባም፡፡ ሐዋርያው፡- “ከተናገርነውም ዋና ነገሩ ይህ ነው፡፡ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፡፡ እርስዋም በሰው ሳይሆን በጌታ የተተከለች ናት” እንዲል /ዕብ.8፡1-2/፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ እንደ ወረደ ግልጽ ነው /ዮሐ.3፡13/፡፡ ሆኖም ግን “ወረደ” የሚለው አገላለጽ ለምልዓተ መለኰቱ ወሰን ለሌለው ለመለኰታዊ ቃል የሚስማማ አይደለም፡፡ ሰው ሆኖ፣ ሥጋ ለብሶ፣ ባጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ ለድኅነተ ዓለም መገለጡን፤ ለሕማም፣ ለሞት፣ ለመሥዋዕትነት መምጣቱን የሚገልጽ እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ሲናገር፡- “ወልድ ዋሕድ እንደ መላእክት ቦታውን የለቀቀ አይደለም፤ በአንድ ፈቃድ ከአባቱ ጋር እያለ ነው እንጂ፡፡ ከአንዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ በተላከ ጊዜ እንደ መላእክት ቦታውን ለቆ የሄደ አይደለም፤ እነዚያ በተላኩ ጊዜ ቦታቸውን ለቀው ይሄዳሉና፡፡ በምልዓት ሳለ እንደ መላእክት ቦታውን ሳይለቅ ሥጋን ተዋሐደ እንጂ” ይላል /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.3፡153-158/፡፡ ልክ እንደዚሁ “ተቀመጠ” የሚለው ቃልም ሥራዉን መጨረሱን፣ ወደ ቀደመ ክብሩ መመለሱን፣ ድኅነተ ዓለም መፈጸሙን የሚያመለክት እንጂ እንደተናገርነው ለምልዓተ መለኰቱ ቦታ ተወስኖለት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንትም ይህን ሲያመሰጥሩት፡- “ጌታ ከምልዓተ መለኰቱ የተወሰነበት ወቅት ኑሮ መንበረ ክብሩን ተቆጣጠረ ወይም ከመለኰታዊ ክብሩ ተራቁቶ ኑሮ ወደ መለኰታዊ ክብሩ በተመለሰ ጊዜ መለኰታዊ ክብሩን ተቆጣጠረ ማለት ሳይሆን ሰውን ለማዳን ሰው ሆኖ ሰማያዊ ያልነበረውን (ክብር የለሽ የነበረውን) የሰውን ባሕርይ ማክበሩንና በእርሱ ክብር መክበራችን፣ በክብር ቦታ መቀመጣችን፣ የሰው ልጅ ሁሉ በክርስቶስ መክበሩን ነው” ይላሉ /ኤፌ.2፡6-7/፡፡ “በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለበጉ ይሁን” አሜን /ራዕ.5፡14/፡፡
3. በገዛ ደሙ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የገባ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉዩ ሊቀ ካህናት ለኃጢአት መሥዋዕት ወይፈን ለሚቃጠል መሥዋዕትም አውራ በግ ይዞ የዚህ ዓለም (አፍአዊ) ወደ ሆነችው መቅደስ ይገባ ነበር፡፡ አገልግሎቱም ሁሉ ምድራዊ ዓለማዊ ነበር፤ ሥጋን እንጂ ነፍስን መቀደስ የማይቻለው ነበር /ዘሌ.16፡3/፡፡ እንደ ወንበዴ ከወንበዴዎች ጋር የተሰቀለው፣ የተናቀው፣ ገሊላዊ፣ የዓለምንም ኃጢአት ያስወገደው የእግዚአብሔር በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እንደተጻፈ በደመ በግዕ በደመ ላህም ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የገባ አይደለም፡፡ ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ ተወካፌ መሥዋዕት (መሥዋዕት ተቀባይ)፣ ራሱ ይቅር ባይ ሊቀ ካህናት አስታራቂ መሥዋዕት አቅራቢ ሆኖ ገባ እንጂ /ዮሐ.1፡29, St. Augustine, On Ps. 65./፡፡ ሐዋርያው፡- “ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን የዘለዓለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም” እንዲል /ዕብ.9፡11-13/፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጠቀም ብሎ ሳይሆን ቅዱሳንን ሊያገለግል ደሙን ይዞ የገባባት ቅድስተ ቅዱሳን ማን ናት? “ኢየሱስ ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ በምትበልጠውና በምትሻለው በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንጂ በዘር በሩካቤ ባልተከፈለች  /ማቴ.1፡20/ በሥጋው መሥዋዕት በኵል /ዕብ.10፡20/ ስለ እኛ ይታይ ዘንድ፣ እንደ አይሁድ ሐሳብ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ዕቅድ  መስቀል ላይ በሠዋው አንድ መሥዋዕት ከራሱ ከባሕርይ አባቱና ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያስታርቀን ዘንድ የገባባት ቅድስተ ቅዱሳን እዝነ አብ (የአብ ጀሮ) ገጸ አብ (የአብ ፊት) ናት” /St.John Chrysostom, Homily on the Epistle Of Hebrews, Hom.15፣ ዕብ.9፡24/፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው ጌታችን ወደ እዝነ አብ ወደ ገጸ አብ አቀረበን ስንል (በሥላሴ ዘንድ ተከፍሎ ስለሌለ) የታረቅነው ከሥላሴ ጋር መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ መሥዋዕት ተቀባዩ አብ ብቻ እንዳልሆነ የታወቀ የተረዳ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ሊቃውንትም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ይህን ክፍል በተረጐሙበት አንቀጽ፡- “ለምትመጣው ሕግ ለወንጌል ሊቀ ካህናት ሆኖ የመጣው ክርስቶስ ግን በምክንያተ ዘርዕ ያይደለ እንበለ ዘርዕ ወደተገኘች ወደ ደብተራ ርእሱ፣ በሰው ፈቃድ ያይደለ በእርሱ ፈቃድ ወደ ተተከለች ደብተራ መስቀል ደመ ላህም፣ ደመ ጠሊን ይዞ የገባ አይደለም፤ ደሙን ይዞ አንድ ጊዜ ወደ እዝነ አብ ወደ ገጸ አብ ገባ እንጂ” ብለዋል /የቅዱስ ጳውሎስ መጽሐፍ ንባቡ ከነትርጓሜው፣ ገጽ 441/፡፡ ተወዳጆች ሆይ! አንድ ፍጹም ልንረሳው የማይገባ መሠረታዊ ነገር አለ፡፡ እርሱም ምን እንደሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይነግረናል፡- “የጌታችን አገልግሎቱ እዚህ ምድር በመስቀል ላይ የተፈጸመ ቢሆንም እንደ ቀደሙት ሊቃነ ካህናት ምድራዊ አገልግሎት አልነበረም፤ ሰማያዊ እንጂ፡፡ ለምን ቢሉ ምእመናን በእርሱ አምነን መጠመቅን ገንዘብ አድርገን የሰማያውያን ሥራ እየሠራን የእርሱ ልጆች እንሆናለንና፡፡ ሐሳባችንም ሀገራችንም መንግሥተ ሰማያት ነውና፡፡  ምስጋናችንም ከመላእክት ጋር ኅብረት አንድነት ያለው ሰማያዊ ነውና፡፡ መሥዋዕታችንም እንጨት ማግዶ እሳት አንድዶ የሚቀርብ የላም የበግ ደም ሳይሆን ሰማያዊው መሥዋዕት (ክርስቶስ) ነውና፡፡ ሕጉም (ወንጌሉም) ክህነቱም ሰማያዊ ነውና፡፡ መሥዋዕታችን እንደ ቀደመው ኪዳን መሥዋዕት አመድና ጢስ እንዲሁም መዓዛ ሆኖ የሚቀር ሳይሆን ንጽሐ ሥጋ ንጽሐ ነፍስ የሚሆን ክብር ነውና፡፡ ይህን የምናከናውንበት ሥርዓተ ቅዳሴአችንም ሰማያዊ ነውና” /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ድር.14፡58-77/፡፡ የስነ መለኰት ምሁራንም እንዲህ ሲሉ ይህን የቅዱሱ ሐሳብ ያጐለሙሱታል፡- “ምንም እንኳን በምድራዊቷ ድንኳን (ቅድስት ቤተ ክርስቲያን) ብንሆንም ክርስቲያኖች ወደዚሁ ቅዱስ መሥዋዕት (ወደ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ) በምንቀርብበት ሰዓት ወደ ቅድስተ ቅዱሳን እንገባለን፤ ማንነታችን ከጊዜና ከቦታ ቀመር ውጪ /Kairos/ ይሆናል፡፡ እዚህ ሆነን የመንግሥተ ሰማያትን ኑሮ እንለማመዳለን፡፡ ከመለኰታዊ ባሕርይ ተካፋይ እንሆናለን፡፡ ትላንት፣ ዛሬና ነገ ከሚለው ማንነታችን /Chronos/ ወጥተን “አሁን” /Kairos/ ወደሚለው ማንነታችን እንቀየራለን፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ትላንት፣ ዛሬ፣ ነገ የሚሉ አገላለጾች የሉምና፡፡ ወደ ፊት ደግሞ (ዓለም ሲያልፍ) ከጊዜ መፈራረቅ ውጪ ሆነን ለዘለዓለሙ ወደዚሁ ማንነታችን (ወደ Kairos) እንለወጣለን፡፡ ወደ ቅዱስ ቁርባን ስንቀርብ ከጠብና ከበቀል የራቅን እንሁን የሚባልበት ምሥጢርም ማንነታችን ከዚህ ምድር ስለሚለይ ነው፡፡ በሰማያዊ ሕይወት ጠብና በቀል የለምና፡፡ እነዚህን ሳናስወግድ ስንቀርብ ግን ያው እላይ መሆናችን ቀርቶ እታች ነን ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን የተቀበልን መስሎንም ሳንቀበል እንቀራለን፡፡ ሳይገባን ይህን እንጀራ ስለበላን ወይም የጌታን ጽዋ ስለጠጣንም ዕዳ ይሆንብናል” /1ቆሮ.11፡27/፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! ሳምንት ይቀጥላል!!

Monday, July 2, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል ሦስት!


      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
 በክፍል ሁለት ትምህርታችን ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ እግዚአብሔር ሥርዓት ከሰዎች ተመርጠው ከሚሾሙት የብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናት ፍጹም የሚለይባቸውን ነጥቦች ማሳየት ጀምረን ነበር፡፡ የሚምር ነው፤ የታመነ ነው፤ በሰማያት ያለፈ ነው፤ በድካማችን የሚራራልን ነው ብለን አራት ነጥቦችን አይተናል፡፡ ለዛሬም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካቆምንበት እንቀጥላለን፡፡ ቢችሉ አስቀድመው ይጸልዩ!
1. በመሐላ የተሾመ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ መሐላ የማይለወጥ ነገርን ያመለክታል፡፡ አንድ ሰው ይህን አላደርግም እንዲህም አላደርግም ብሎ ከማለ የነገሩን ሓቅነት ያመለክታል፡፡ “ሰዎች ከእነርሱ በሚበልጠው (ሎሌ በጌታው፣ ገረድ በእመቤቷ፣ ደቀ መዝሙር በመምህሩ፣ ልጅ በአባቱ) ይምላሉና ለማስረዳትም የሆነው መሓላ የሙግት (የክርክር የጸብ) ሁሉ ፍጻሜ ይሆናል፤ ስለዚህም እግዚአብሔር የተስፋውን ቃል ለሚወርሱ ፈቃዱ እንደማይለወጥ አብልጦ (አብዝቶ) ሊያሳያቸው ስለ ፈቀደ እግዚአብሔር ሊዋሽ (ሊፈርስ፣ ሊታበል) በማይቻል በሁለት  በማይለወጥ ነገር በፊታችን ያለውን ተስፋ ለመያዝ ለሸሸን ለእኛ ብርቱ መጽናናት ይሆንልን ዘንድ በመሐላ (በሥጋዌው) በመካከል ገባ፤ ይህም ተስፋ እንደ ነፍስ መልሕቅ አለን (ተስፋችንን አጽንተን ለያዝን ለእኛ ልቡናችን እንዳይነዋወጥ እንደ ወደብ የሚያጸናን ፍጹም ደስታ አለን)፤ እርሱም እርግጥና ጽኑ የሆነ ወደ መጋረጃውም ውስጥ የገባ (እንደ መልከ ጼዴቅ ባለ ሹመት ተሹሞ ወደ ውሳጤ መንጦላዕት የገባ የዘላለም አስታራቅያችን ፊተውራርያችን ኢየሱስ ክርስቶስ) ነው” እንዲል /ዕብ.6፡16-19/፡፡ እንግዲያውስ ከሌዋውያን ክህነት በሚበልጥ ክህነት፣ እንደ መልከ ጼዴቅ ክህነት ዘላለማዊ በሆነ ክህነት የተሾመ ሊቀ ካህናት አለን፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ምንም እንኳን በእግዚአብሔር ጥሪ የተመረጡ ቢሆኑም አገልግሎታቸው ጊዜአዊ ስለ ነበረ ያለ መሓላ የተሾሙ ነበሩና፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ከኦሪት ለምትበልጥ ለወንጌል መምህር ለመንግሥተ ሰማይም አስታራቂ ሆኖአልና በመሓላ የተሾመ ዘላለማዊ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያውም ስለዚሁ ሲናገር እንዲህ አለ፡- “እነርሱም ያለ መሓላ ካህናት ሆነዋልና፤ እርሱ ግን፡- ጌታ፡- አንተ እንደ መልከጼዴቅ ሹመት ለዘላለም ካህን ነህ ብሎ ማለ አይጸጸትም ብሎ በተናገረለት ከመሓላ ጋር ካህን ሆኖአልና ያለ መሓላ ካህን እንዳልሆነ መጠን እንዲሁ ኢየሱስ ለሚሻል ኪዳን ዋስ ሆኖአል /ዕብ.7፡20-22/፡፡ በዚህም ኦሪት ሥርየተ ኃጢአትን ማሰጠት ስላልቻለች እንደተሻረች ወንጌል ግን ማዳን ስለቻለች፣ ሥርየተ ኃጢአትን ማሰጠት ስለቻለች ሕልፈት ሽረት እንደሌለባት አወቅን፤ ተረዳን፡፡ ካህኑም አገልግሎቱም እንደዚሁ፡፡ ለምን ቢሉ ያለ መሓላ ከተሾሙት የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ይልቅ በመሓላ የተሾመ ሊቀ ካህናት ወልደ አብ ወልደ ማርያም ኢየሱስ ይበልጣልና፡፡  
2. የማይለወጥ ክህነት ያለው ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የቀደሙት ሊቃነ ካህናት ያለ መሓላ ለተሠራችው ሕገ ኦሪት የተሾሙ ስለ ነበሩ አንድም መዋትያን ስለ ነበሩ ካህናት የሆኑ ብዙዎች ናቸው፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በመሓላ ለተሠራችው ወንጌል የተሾመ ስለሆነ አንድም ሞትን በሞቱ ገድሎ ተነሥቶ በሕይወት የሚኖር ሥግው ቃል ስለሆነ ወራሽ የሌለው አንድ ነው፡፡ ክህነቱም (ኃጢአት የማሥተስረይ ችሎታውም) የባሕርዩ ስለ ሆነ በሞት (ሞት ሊያሸንፈው ስላልቻለ) አይለወጥም፡፡ የባሕርዩ የሆነውን ለእነዚያ በጸጋ ሰጥቷቸው ነበርና ሥጋ ለብሶ በክህነት ሲገለጥ ባሕርያዊ ሥልጣኑ የማይሻር ሆነ፡፡ ሐዋርያውም ይህን አስመልክቶ ሲናገር፡- “እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸው፤ እርሱ ግን ለዘለዓለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው አለን /ዕብ.7፡23-24/፡፡
3. ሞትን አሸንፎ በሕይወት የሚኖር ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያው እንዲህ ይላል፡- “የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና፡፡ ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል” /ዕብ.7፡25/፡፡ ካቶሊክ ሳትታሰብ ፕሮቴስታንትም ሳትታለም ከ325 እስከ 389 ዓ.ም የነበረውና የቀጰዶቅያ አውራጃ ለምትሆን የቂሳርያ ሊቀ ጳጳስ የሆነው ሊቁ ቅዱስ ጐርጐርዮስ ዘእንዚናዙ ይህን ሲተረጕመው እንዲህ ይላል፡- “ይህ ቃል የሚያመለክተን የጌታችን አስታራቂነቱን ነው፡፡…  ምክንያቱም መጽሐፍ እንደሚል አንድ እግዚአብሔር አለና፣ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው  (ሰው ሆኖ ሰውና እግዚአብሔርን ያስታረቀ) ደግሞ አንድ አለ፣ እርሱም (ለሁሉ ቤዛ አድርጎ ራሱን አሳልፎ ለሞት ለሕማም የሰጠ) ሰው የሆነው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው /1ጢሞ.2፡5-6/፡፡ አሁንም ይህ ሥግው ቃል ከመቃብር በላይ ነው፡፡ እንዲህም ስለሆነ “በአብ ዘንድ ጠበቃ አለን” እንላለን /1ኛ ዮሐ.2፡1/፡፡ ሆኖም ግን ይህን በአብ ፊት በመውደቅና በመነሣት የሚያደርገው አይደለም፤ በዕለተ ዐርብ በተቀበለው መከራ ባደረገው ተልእኮ እንጂ”  /On The Son, Theological Oration, 4(30):14/፡፡ ከ347 እስከ 407 ዓ.ም የነበረውና የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ የሆነው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም እንዲህ ይላል፡- “የቀደሙት ሊቀነ ካህናት መዋትያን ስለ ነበሩ ብዙ ናቸው፡፡ እርሱ ግን የማይሞት ሕያው ስለሆነ አንድ ነው፡፡ የማይሞትም ስለ ሆነ እርሱን አምነው የሚመጡትን ሁሉ ሊያድናቸው ይቻለዋል፡፡ እንደምንስ ያድናቸዋል? የሚል ሰው ካለም “በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ ነው” ብለን እንመልስለታለን፡፡ በሃይማኖት በንስሐ ወደ እርሱ የሚቀርቡትን የሚያድናቸው በዕለተ ዐርብ ብቻ አይደለም፡፡ ከዚያ በኋላም ጭምር እንጂ፡፡ በወደደበት ጊዜም ለመነላቸው፡፡ ሁል ጊዜ ይለምናል ብሎ የሚያስብስ ከቶ እንደምን ይኖራል? ጻድቃንስ እንኳ አንድ ጊዜ በለመኑት ልመና የሚሹትን የሚያገኙ አይደሉምን?… ሐዋርያውም ሁል ጊዜ ቁሞ የሚያገለግል እንዳያስመስሉት በማሰብ በመትጋት መሥዋዕት አንድ ጊዜ እንደሠዋ አስረዳ፡፡ አንድ ጊዜ ሰው እንደ ሆነ አንድ ጊዜ ተሾመ፤ አንድ ጊዜ እንደ ተሾመ አንድ ጊዜ አገለገለ፡፡ ሰው በሆነ ጊዜ የሰውነትን ሥራ በመሥራት ጸንቶ እንዳልኖረ ሁሉ ባገለገለ ጊዜም በማገልገል ጸንቶ አልኖረም፡፡ አሁን ቢያገለግል ኖሮ ሐዋርያው ቆመ እንጂ ተቀመጠ ባላለ ነበርና፡፡ መሥዋዕቱ ቁርጥ ልመናውን አንድ ጊዜ ወደ እዝነ አብ (በአብ ጀሮ) ወደ ገጸ አብ (በአብ ፊት) የደረሰች ስለሆነች እንደ ቀደሙት ሊቃነ ካህናት ሁል ጊዜ ሊያገለግል አያስፈልገውም” /Homily on the Epistle of Hebrews, Hom.13/፡፡ የኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ትርጓሜም ተመሳሳይ ነው፡- “በዕለተ ዐርብ ባደረገው ተልእኮ እስከ ምጽአት ድረስ ሲያድንበት የሚኖር ስለ ሆነ በእርሱ አስታራቂነት ወደ እግዚአብሔር የቀረቡትን ማዳን ይቻለዋል” /የቅዱስ ጳውሎስ መጽሐፍ ንባቡ ከነ ትርጓሜው፣ ገጽ 434/፡፡ እንግዲያውስ ተወዳጆች ሆይ! “ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራል” የሚል ጥሬ ምንባቡን ብቻ በመያዝ እንዳይሳሳቱ ይጠንቀቁ፡፡ ይህ ማለት አስቀድመን እንደነገርንዎት የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ የዕለተ ዐርብ የማስታረቅ አገልግሎት ከአዳም መፈጠር ጀምሮ እስከ ዕለተ ዐርብ ላሉት ሁሉ ብቻ ሳይሆን እስከ ዕለተ ምጽአት የሚፈጠረው ፍጥረት ሁሉ በዚሁ የዕለተ ዐርቡ የማስታረቅ አገልግሎት እያመነ እንደሚድን ደሙም የማስታረቅ ችሎታ እንዳለው የሚገልጽ ነውና /ዮሐ.17፡20-21/፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ጊዜ የሠዋው መሥዋዕት እንደ ብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት መሥዋዕት ተረፈ ኃጢአት (ያልተደመሰሰ ኃጢአት) አስቀርቶበት አሁን ያንን ለማስተስረይ የሚወድቅ የሚነሣ አይደለምና፡፡ ጸሎቱና መሥዋዕቱ ምልአተ ኃጢአትን (ኃጢአትን ሁሉ) ለመደምሰስ አንድ ጊዜ ተፈጽሟልና /ዮሐ.19፡30/፡፡ ስለዚህ ይማልድልናል ስንል “የዕለተ ዐርቡ ቤዛነት፣ ካሣ፣ ሞት፣ ደም መፍሰስ አዲስና በየዕለቱ ንስሐ የሚገቡትን የሚያቀርብ የሚያድን ነው” ማለት መሆኑን ልንረዳ ያስፈልጋል፡፡  ስለዚህም ነው ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች “ከእርሱ ውጪ ሌላ ሊቀ ካህን የለንም፤ ከቅዱስ ሥጋዉና ከክቡር ደሙ ውጪ ሌላ በየቀኑ የምናቀርበው መሥዋዕት የለንም” የምንለው፡፡ ክህነቱ የማይለወጥ፣ መሥዋዕቱም አንድ ጊዜ ቀርቦ በጊዜ ብዛት የማይበላሽ ሕያው አሁንም ትኵስ ነውና፡፡ ትኵስ መባሉም ነፍስ ስላለው ሳይሆን መለኰት የተዋሐደው ስለሆነ ነው፡፡
4. በእርሱ በኵል (እርሱን አምነው) ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡትን ሊያድን የሚችል ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ሐዋርያው እንዲህ ይላል፡- “የማይለወጥ ክህነት አለው፤ ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል” /ዕብ.7፡25/፡፡ ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጌታችን ራሱ እንዲህ ብሏል፡- “እውነት እውነት እላችኋለሁ እኔ የበጎች በር (ደጅ) ነኝ… በሩ እኔ ነኝ በእኔ የሚገባ (በእኔ ያመነ) ቢኖር ይድናል ይገባልም ይወጣልም መሰማርያም ያገኛል (ክብረ ሥጋን ክብረ ነፍስን ያገኛል፤ መንግሥተ ሰማያትንም ይወርሳል)” /ዮሐ.10፡7፣9/፤ “እኔ መንገድና እውነት ነኝ (የሕይወትና የጽድቅ መንገዷ እኔ ነኝ) በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም (እኔን ልጅ ካላለ በቀር አብን አባት የሚለው የለም አንድም በእኔ የማያምን ከአብ ጋር መታረቅ አይችልም)” /ዮሐ.14፡6-7/፡፡ እውነት ነው! የሕይወት መሥመር ክርስቶስ ነውና ክርስቶስን አምኖ የሚኖር ሰው ሕይወትን ያገኛል፡፡ ማንም ይሁን ማን ክርስቶስን ካላመነ ቢጾምም ቢጸልይም ያለ ክርስቶስ ዋጋ የለውም፤ በክርስቶስ ካልሆነ በቀር ዓለም በራሱ ሕይወት የለውም፤ በክርስቶስ ቤዛነት የማያምን በሌላ በምንም መንገድ አይድንም፡፡
5. ድካም የሌለበት ፍጹም ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ድካምን የሚለብሱ እንደነበረ መጽሐፍ የሚሰክረው የታወቀ የተረዳ እውነት ነው፡፡ ይህም በጣም የተገለጠ ድካም በታየባቸው በኤሊ ልጆች መረዳት እንችላለን፡፡ አፍኒንና ፊንሐስ የተባሉ የኤሊ ልጆች በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ለመሥዋዕት ከሚቀርበው ሥጋ ለግል ጥቅማቸው በማዋል እግዚአብሔርን ያሳዝኑ ነበር፡፡ ይህም ሳይበቃቸው በመገናኛው ድንኳን ከሚያገለግሉ ሴቶች ጋር ያመነዝሩ ነበር /1ሳሙ.2፡12-22/፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ጻድቅና ቅን፣ ነቀፋ የሌለበት እውነተኛ፣ ከኃጢአት ሁሉ ፈጽሞ የራቀ የተለየ ከሰማያትም ከፍ ያለ ነው /ዕብ.7፡26/፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም ይህን ሲመሰክሩ እንዲህ ይላሉ፡- “በአፉም ተንኰል አልተገኘበትም” /ኢሳ.53፡9/፤ “ኃጢአት ያላወቀው” /2ቆሮ.5፡21/፤ “እርሱ ኃጢአትን አላደረገም” /1ጴጥ.2፡22/፤ “በእርሱ ኃጢአት የለም” /1ዮሐ.3፡5/፡፡ ጌታችንም ራሱ እንዲህ ብሏል “ከእናንተ ስለ ኃጢአት (ኃጢአት ሠርተሃል ብሎ) የሚከሰኝ ማን ነው?” /ዮሐ.8፡46/፡፡ ለሞት አሳልፈው የሰጡት ተቃዋሚዎቹም ሳይቀሩ ይህን መስክረዋል፡- “ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ” /ማቴ.27፡4/፤ “በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም” /ሉቃ.23፡4/፡፡  
6. ስለ ራሱ መሥዋዕት የማያሻው ነውር የለሽ ፍጹም ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ዕሩቅ ብእሲና እንደ ማንኛውም ሰው ኃጢአተኞች ስለነበሩ ሕዝቡን ከእግዚአብሔር ጋር በመሥዋዕት በጸሎት ከማስታረቃቸው በፊት ስለ ራሳቸው ቁርባን መሥዋዕት ያቀርቡ ነበር /ዘሌ.9፡7፣ ዘሌ.16፡6፣ ዕብ.5፡3-4/፡፡ ሊቀካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን አስቀድመን እንደተናገርነው በባሕርይው ድካም የሌለበት ቅዱስ፤ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለበት ንጹሕ፤ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን ሳይጐድልበት የሚያድል ባዕለ ጸጋ፤ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን የሚያርቅ ቡሩክ፤ ከኃጢአተኞችም የተለየና ነውር የሌለበት ፍጹም ስለሆነ “እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈለገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና” /ዕብ.7፡27/፡፡ 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር (ሳምንት ይቀጥላል)!

Monday, June 25, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል ሁለት!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
    በክፍል አንድ ትምህርታችን ከሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ስለ ሊቀ ካህናት በስፋትና በጥልቀት የጻፈልን የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ እንደሆነ፤ የዚህ ምክንያትም ምን እንደሆነ እና  ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህን ትምህርት አብዝታ እንደምታስተምር ከአዋልድ መጻሕፍቶቿ ጠቅሰን ነበር ያቆምነው፡፡ ለዛሬ ደግሞ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ እግዚአብሔር ሥርዓት ከሰዎች ተመርጠው ከሚሾሙት የብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናት ፍጹም የሚለይባቸውን ነጥቦች ማሳየት እንጀምራለን፡፡ አንባብያን ትምህርቱን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር እያመሳከሩ ቢያነቡት የበለጠ ይጠቀማሉ፡፡

1. የሚምር ሊቀ ካህናት ነው፡፡ መጽሐፍ ይህን ሲመሰክር፡- “የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም፡፡ ስለዚህ የሕዝብን ኃጢአት ለማስተስረይ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ የሚምርና የታመነ ሊቀ ካህናት እንዲሆን በነገር ሁሉ ወንድሞቹን መምሰል ተገባው” ይላል /ዕብ.2፡16-17/፡፡ አዎ! የዘመናት ጌታ እንደ ሰዎች ዘመን ተቈጠረለት፤ በልደት በሕማም በሞት ወንድሞቹን መምሰል ተገባው፡፡ ባሕርያችንን የተዋሐደው ሌላ ምንም ምን ምክንያት የለውም፡፡ እኛን ከማፍቀሩ የተነሣ ዘመድ ሊሆነን አንድም እኛን ይቅር ለማለት ኃጢአታችንንም ለማስተስረይ እንጂ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል፡- “ተመለከተን፤ እነሆም ጠላቶቹ ሆነን ተገኘን፡፡ ወደ እርሱ ያቀርበን ዘንድ የሚችል ኪዳንም ቢሆን መሥዋዕትም ቢሆን ፈጽሞ አልነበረንም፡፡ ስለዚህም አዘነልን፤ ራራልን፡፡ ከመላእክትም ይሁን ከኃይላት ወገን ሊቀ ካህናት አልሾመልንም፤ እርሱ አንዱ ወደዚህ ዓለም ወርዶ ባሕርያችንን ባሕርይ አድርጐ የሚምር ሊቀ ካህናት (አስታራቂ) ሆነን እንጂ” /ሃይማኖተ አበው 62፡13/፡፡ ይህም በመዋዕለ ሥጋዌው ተመልክተነዋል፡፡ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ሲፈርዱባቸው የነበሩ ሰዎች፣ “Public Sinners” ብለው ከማኅበረሰቡ ያገለሉዋቸውን ሰዎች አዛኙ ሊቀ ካህናችን ሲያገኛቸው ግን “እኔም አልፈርድብሽም”፤ “ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል” ይላቸዋል /ዮሐ.8፡11፣ ሉቃ.7፡48/፡፡ ስለዚህ ሊቀ ካህናችን መሓሪ ነው፡፡

2. የታመነ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ሊቃነ ካህናት ይጐድላቸው ከነበረው ነገር አንዱ ታማኝነት ነበር፡፡ ለምሳሌ አሮንን ብንመለከት በእግዚአብሔር ፊት ታማኝነት ይጐድለው ነበር፡፡ መጽሐፍ ይህን ሲመሰክር፡- “እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን። በእስራኤል ልጆች ፊት ትቀድሱኝ ዘንድ በእኔ አላመናችሁምና ስለዚህ ወደ ሰጠኋቸው ምድር ይህን ጉባኤ ይዛችሁ አትገቡም አላቸው” ይላል  /ዘኅ.20፡12/፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የእኛን ኃጢአት ለማሥተስረይ ነውርን ንቆ መከራውን አቃሎ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ ሐፍረተ መስቀልን ይሁንብኝ ብሎ የተቀበለ ታማኝ ሊቀ ካህናት ነው /ዕብ.12፡2/፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ይህን ሲያብራራው፡- “በእውነት የአብርሃምን ባሕርይ ነሣ እንጂ የነሣው የመላእክትን አይደለም።  ስለዚህ የሕዝብን ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የሚምርና የታመነ ሊቀ ካህናት እንዲሆን በነገር ሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል ተገባው።  መከራ የሚቀበሉትን ሕዙናነ ልብ ይረዳቸው ዘንድ እርሱ ራሱ ተፈትኖ መከራን ተቀበለ። ስለዚህ፥ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ፥ የሃይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ፤ እርሱ ለሾመው የታመነ ነበረና” ይላል /Discourses against Arians, 2:8/፡፡

3. በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት የሚገቡት ወደ ምድራዊት ድንኳን ነበር፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በሰማያት ያለፈ (ውሳጤ መንጦላዕት የገባ) ትልቅ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ኢያሱ ወልደ ነዌ ሊቀ ካህናቱና ሌዋውያን ካህናቱ ከፊት ቀድመው ታቦቱ ሕጉን ተሸክመው ባይቀድሙ ኖሮ ሕዝቡን ፈለገ ዮርዳኖስን አሻግሮ ዕረፍተ ፍልስጥኤምን ባላወረሳቸው ነበር /ኢያሱ.3፡13/፡፡ ታላቁ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ደግ አስታራቂ ይሆነን ዘንድ ወደ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያትም ይዞን ለመግባት እንደ እነዚያ (የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት) ታቦት ሕጉን መሸከም አላስፈለገውም፡፡ እንደ ባሕርይ አምላክነቱ ወደ ገጸ አብ፣ ወደ እዝነ አብ አቀረበን እንጂ /ዕብ.4፡14/፡፡

4. በድካማችን የሚራራልን ሊቀ ካህናት ነው፡፡ የዘመነ ብሉይ ሊቃነ ካህናት ለሚስቱት ሰዎች የሚራሩላቸው ራሳቸው ደግሞ በስንፍናቸው ኃጢአት ስለሚሠሩ ነው፤ የሰውን ድካም በራሳቸው ድካም ስለሚረዱት ነው /ዕብ.5፡2-3/፡፡ እንደዚያ ካልሆነ ግን ሰዎች ናቸውና ስሕተት የሠራው ሰው ኃጢአቱን ካልነገራቸው በቀር ምን ምን በደል እንደሠራ ማወቅ አይቻላቸውም፡፡ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ደክመን ለሠራነው ኃጢአት የባሕርይ አምላክ እንደመሆኑ ምን ምን ድካም እንዳለብንም ስለሚያውቅ ይራራልናል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን እነዚህን ሁሉ ሰው ሆኖ በገቢር አይቶአቸዋል፡፡ የእኛን ስደት ተሰዶ አይቶታል፤ የእኛ መሰደብ ተሰድቦ አይቶታል፤ የእኛ መወቀስ ተወቅሶ አይቶታል፤ የልጆቹ መገረፍ ተገርፎ ብቻ ሳይሆን ተሰቅሎ አይቶታል፡፡ “ስለዚህ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም” /ዕብ.4፡15/፡፡

       ይቆየን! (ሳምንት ይቀጥላል!)

Tuesday, June 19, 2012

የሃይማኖታችን ሊቀ ካህናት- ክፍል አንድ!!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!   
    ከሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ስለ ሊቀ ካህናችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ በስፋትና በጥልቀት የምናገኘው በዕብራውያን መልእክት ነው፡፡ ሐዋርያው መልእክቱን የጻፈበት ዓላማም በአጭሩ እንዲህ ቀርቧል፡- በይሁዳ ሀገርና በብሔረ አሕዛብ ሁሉ ያሉ ዕብራውያን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንና ደቀ መዛሙርቱን ወንጌልን በማስተማራቸው አጽንተው ይጠልዋቸው ነበር፡፡ ጌታ ካረገ በኋላ ግን በሐዋርያት ቃል የሚደረገውን ተአምራት ባዩ ጊዜ ከእነርሱ ብዙዎች በጌታችን ስም አመኑ /ሐዋ.2 ሙሉውን ይመልከቱ/፡፡ ሆኖም ግን ሕገ ኦሪትን ከሕገ ወንጌል ይልቅ አብልጠው መጠበቃቸው አልተዉም፡፡ በሌላ አገላለጽ ሕገ ወንጌልን ለሕገ ኦሪታቸው ተጨማሪ ሕግ አድርገዋት ነበር፡፡

  ሐዋርያትም ሃይማኖተ ወንጌል በዓለሙ ሁሉ እስኪስፋፋ ድረስ ኦሪትን ከወንጌል ጋር እንዲጠብቁ ተዋቸው እንጂ “ኦሪታችሁን ፈጥናችሁ ልቀቁ” አላልዋቸውም ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ አይሁድ አሕዛብን ለጓደኝነት ይጸየፍዋቸው ምግባቸውም ከመብላት ይከለከሉ ነበር፡፡  ሐዋርያት ወንጌልን ሲያስተምርዋቸው ተአምራት ሲያደርጉላቸው አይተው ቢያምኑም ተገዘሩ፤ ሕገ ኦሪትን ጠብቁ ስላላልዋቸው ፍጹም ቅናት አደረባቸው፡፡ የኦሪታቸውና የሌዋውያን ክህነት የላሙን፣ የበሬዉን፣ የበጉን፣ የፍየሉን መሥዋዕትና በጠቅላላው የአባቶቻቸውን ሥርዓት ማለፍ ባሰቡ ጊዜ እጅግ አዘኑ፡፡ ከጥንት ጀምሮ ለእነርሱ ብቻ ይነገር የነበረው ተስፋ ለሁሉም እንደሆነ ባሰቡ ጊዜ እጅግ ታወኩ፡፡ ከዚህ በኋላ በአንድነት መከሩና ከአሕዛብ ወገን በወንጌል ያመኑትን “ወንጌል ያለ ኦሪት ጥምቀት ያለ ግዝረት አትረባምና ተገዘሩ ሕገ ኦሪትንም ጠብቁ” እያሉ ዓለምን የሚያውኩ ሐሰተኛ ወንድሞችን ወደ አንጾክያ ሰደዱ፡፡ የግብረ ሐዋርያት ጸሐፊ “ከይሁዳ ሀገርም የወረዱ ሰዎች እንደ ሙሴ ሕግ ካልተገዘራችሁ ልትድኑ አትችሉም እያሉ ወንድሞችን ያስተምሩ ነበር” እንዲል፡፡

  ስለዚህም በአንጾክያ ያሉ አሕዛብ እጅግ ታውከው ጳውሎስንና በርናባስን ተከራከሯቸው፡፡ ስለዚህ ክርክር ጳውሎና በርናባስ ከእነርሱም አንዳንዶች ሌሎች ሰዎች ወደ ሐዋርያት ወደ ቀሳውስትም ወደ ኢየሩሳሌም ይወጡ ዘንድ ተቈረጠ።

  ወደ ኢየሩሳሌምም በደረሱ ጊዜ ቤተ ክርስቲያንና ሐዋርያት ቀሳውስትም ተቀበሉአቸው፤ እግዚአብሔርም በአሕዛብ ዘንድ ተአምራት እንዳደረገላቸው አሕዛብም ሳይገዘሩ መንፈስ ቅዱስ እንደ ወረደላቸው ቢነግሯቸው ሐዋርያትና ቀሳውስቱ እጅግ ደስ አላቸው፡፡

  ከፈሪሳውያን ወገን አምነው የነበሩ አንዳንድ ሰዎች ግን ተነሥተው ወደ ሐዋርያት ሔዱና “ከአሕዛብ ያመኑትን ትገርዙአቸው ዘንድና ሕገ ኦሪትንም እንዲጠብቁ ታዙአቸው ዘንድ ይገባል” አሏቸው፡፡ ሐዋርያትና ቀሳውስት ግን በክርስትናው ታሪክ የመጀመርያው በሆነው በዚሁ ጉባኤያቸው “ከጣዖት ወደ ወንጌል በተመለሱ አሕዛብ ሸክም አታክብዱ፤ ሁላችንም በጸጋ እግዚአብሔር በወንጌል አንድ እንሆናለን እንጂ አባቶቻችን እኛም ያልቻልነውን ጽኑ ሸክም አታሸክሟቸው፡፡ ለጣዖት የተሠዋውን፣ ሞቶ ያደረውን፣ በደም የታነቀውን ከመብላትና ከዝሙት

Sunday, May 27, 2012

አንድ ፕሮቴስታንት ለጠየቀኝ የተለያዩ ጥያቄዎች በጽሑፍ የሰጠሁት ምላሽ

        በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!  

   1. “በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ፥ ጠላቶቹም አፈር ይልሳሉ። የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የዓረብና የሳባ ነገሥታት እጅ መንሻን ያቀርባሉ።”  እና “የግመሎች ብዛት፥ የምድያምና የጌፌር ግመሎች፥ ይሸፍኑሻል፤ ሁሉ ከሳባ ይመጣሉ፥ ወርቅንና ዕጣንን ያመጣሉ የእግዚአብሔርንም ምስጋና ያወራሉ።” ተብሎ በነብያቱ የተነገረውን ትንቢት በቀጥታ “ወደ ቤትም ገብተው ሕፃኑን ከእናቱ ከማርያም ጋር አዩት፥ ወድቀውም ሰገዱለት፥ ሣጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን ከርቤም አቀረቡለት።” ተብሎ ሲፈጸም ስለምንመለከተው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ. ጌታ ሲወለድ በቤተልሔም ተመሠረተች ቢባል ያስኬዳል /መዝ.71፡9-10፣ ኢሳ.60፡6፣ ማቴ.2፡1-11/፡፡ በኋላ ደግሞ የሐዋርያት ሥራ ጸሐፊ እንደሚነግረን፡- “የጌታም መልአክ ፊልጶስን። ተነሥተህ በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ ወደሚያወርደው ምድረ በዳ ወደ ሆነ መንገድ ሂድ አለው።ተነሥቶም ሄደ። እነሆም፥ ህንደኬ የተባለች የኢትዮጵያ ንግሥት አዛዥና ጃንደረባ የነበረ በገንዘብዋም ሁሉ የሠለጠነ አንድ የኢትዮጵያ ሰው ሊሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር፤ሲመለስም በሰረገላ ተቀምጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ያነብ ነበር። መንፈስም ፊልጶስን። ወደዚህ ሰረገላ ቅረብና ተገናኝ አለው። ፊልጶስም ሮጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ሲያነብ ሰማና። በውኑ የምታነበውን ታስተውለዋለህን? አለው። እርሱም። የሚመራኝ ሳይኖር ይህ እንዴት ይቻለኛል? አለው። ወጥቶም ከእርሱ ጋር ይቀመጥ ዘንድ ፊልጶስን ለመነው።ያነበውም የነበረ የመጽሐፉ ክፍል ይህ ነበረ፤ እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፥ የበግ ጠቦትም በሸላቹ ፊት ዝም እንደሚል፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። በውርደቱ ፍርዱ ተወገደ፤ ሕይወቱ ከምድር ተወግዳለችና ትውልዱንስ ማን ይናገራል?  ጃንደረባውም ለፊልጶስ መልሶ። እባክህ፥ ነቢዩ ይህን ስለ ማን ይናገራል? ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ? አለው። ፊልጶስም አፉን ከፈተ፥ ከዚህም መጽሐፍ ጀምሮ ስለ ኢየሱስ ወንጌልን ሰበከለት። በመንገድም ሲሄዱ ወደ ውኃ ደረሱ፤ ጃንደረባውም። እነሆ ውኃ፤ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምንድር ነው? አለው። ፊልጶስም። በፍጹም ልብህ ብታምን፥ ተፈቅዶአል አለው። መልሶም። ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ አምናለሁ አለ። ሰረገላውም ይቆም ዘንድ አዘዘ፥ ፊልጶስና ጃንደረባው ሁለቱም ወደ ውኃ ወረዱ፥ አጠመቀውም። ከውኃውም ከወጡ በኋላ የጌታ መንፈስ ፊልጶስን ነጠቀው፤ ጃንደረባውም ሁለተኛ አላየውም፥ ደስ ብሎት መንገዱን ይሄድ ነበርና።” ይለናል /ሐዋ.8፡26-39/፡፡ ይህም የሆነው በ34 ዓ.ም. ነው፡፡ በይፋ በጳጳስ መመራት የጀመረችው ግን በ330 ዓ.ም. በአባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን አማካኝነት ነው፡፡
  • “ኦርቶዶክስ” የሚለው ቃል “ኦርቶዶክስያ” ከሚለው የግሪክ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ቀጥተኛ (እምነት) ማለት ነው፡፡ የምስራቅና የኦሬንታል አብያተ ክርስቲያናትም ይጠሩበታል፡፡
  • “ተዋሕዶ” የሚለው ቃል በግሪኩ “Miaphysis” የሚለውን ቃል የሚተካ የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ክርስቶስ ሰው የሆነ አምላክ መሆኑን /ዮሐ.1፡1፣14/፣ መለኰትና ትስብእትም ያለ መለያየት፣ ያለ መቀላቀል፣ ያለ መለያየት ስለ ተዋሐዱ አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ ፈቃድ፣ አንድ ግብር መሆኑን የሚገልጽ ነው፡፡
     

Saturday, May 5, 2012

አንዳንድ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ሰዎች ከአንድ በላይ ሚስት ለምን አገቡ? እንዲህ በማድረጋቸውስ እግዚአብሔር ፈቅዶላቸዋል ማለት ይቻላልን?=+=

በብሉይ ኪዳን ከአንዲት ሚስተ በላይ አግብተዋል ከሚባሉት እነ አብርሃም፣ ያዕቆብ፣ ዳዊት እና ሰሎሞን ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ከአንድ በላይ አግብተዋል ማለት ግን እግዚአብሔር ፈቅዶላቸዋል በሥራቸውም ተደስቷል ማለት አይደለም፡፡ እያንዳንዳቸውን እያሳጠርን መመልከት እንችላለን፡- 1. አብርሃም፡- አብርሃም የደረሰባትና እስማኤልንም የወለደላት አጋር ሚስቱ ሳትሆን ገረዱ የነበረች ናት፡፡ ከእርሷ እንዲወልድ የተደረገው እንኳ ሚስቱ ሣራ ልጅ ስላልነበራት አስገድዳው እንጂ እርሱ ራሱ ሊደርስባት ፈልጎ አልያም ደግሞ እግዚአብሔር ይህን እንዲያደርግ ስለፈቀደለት አልነበረም፡፡ አብርሃም ይህን ያደረገው ዝሙት ለመፈጸም ወይም ሌላ ሚስት ለመጨመር ብሎ ሳይሆን የሚስቱን ቃል ሰምቶ ነው /ዘፍ.16፡3/፡፡ ሊቃውንት ሣራ አብርሃምን ለምን እንዳስገደደችው ሲያመሰጥሩት፡- እግዚአብሔር “ከጉልበትህ የሚወጣ ልጅ እንጂ ከአንተ ጋር ያለው ባርያ አይወርስህም” የሚል ቃል ገብቶለት ስለነበረ /ዘፍ.15፡4/ እርሷ ደግሞ ልጅ ስላልነበራትና እግዚአብሔር የገባውን ኪዳን ያስቀረ ስለመሰላት በሰውኛ ጥበብ ልጅ እንዲወልድ ማድረጓ ነበር ይላሉ፡፡ አብርሃም በመጨረሻ ያገባት ሚስት ኬጡራ ትባላለች /ዘፍ.25፡1/፡፡ ነገር ግን ኬጡራን ያገባት ሣራ እያለች ሳይሆን ከሞተች በኋላ ነበር፡፡ ይህ ደግሞ በመሐመዳውያን ዘንድ የምናየው ዓይነት አይደለም፡፡ 2. ያዕቆብ፡- በዘፍጥረት መጽሐፍ ያዕቆብ ራሔልንና ሊያን እንዳገባ እናነባለን፡፡ ነገር ግን ያዕቆብ ሊያን ያገባት በአጐቱ በላባ አታላይነነት እንጂ እርሱ ስለፈለገ ወይም ደግሞ እግዚአብሔር ስለፈቀደለት አልነበረም /ዘፍ.29፡25/፡፡ 3. ዳዊት፡- መጽሐፍ ቅዱስ የእውነት ሚዛን ስለሆነ ዳዊት በቅድስና በተመላለሰባቸው ጊዜያት ከአንበሳ አፍ በጐችን ማስጣሉ፣ በአንዲት ጠጠር ሕዝበ እስራኤልንና እግዚአብሔርን የወቀሰ ጐልያድን መግደሉ፣ ሳውልን በይቅርታ ማሸነፉ፣ ሲሞት እንኳን “እሰይ እንኳን ሞተ” ሳይሆን ማልቀሱንና ማዘኑን፣ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ዛሬ በተለይ ለኢትዮጵያውያን ልዩ ምግብ የሆነውን መዝሙር መዘመሩ ቢጽፍልንም ከዚያ በኋላ ያደረገውን ኃጢአትም አያስቀርብንም፡፡ እናም ዳዊት ወደ ንግሥና ከወጣ በኋላ የሰውነት ድካም ታይቶበታል፡፡ ከአንድ ኃጢአት ወደ ሌላ ኃጢአት ሲሸጋገርም እንመለከታለን፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም፡- “ስንፍና ሕሊናንና አስተሳሰብን ያደነዝዛል፤ የማይወዱትንም ኃጢአት እንዲያደርጉ በርን ይከፍታል” እንዳለው ዳዊት በዚያን ጊዜ ከአሞናውያን ጋር በነበረው ጦርነት ሠራዊቱን አዝምቶ መጸለይ ሲገባው እርሱ በስንፈና አልጋ ተኝቶ ነበር፡፡ መተኛቱም ሳያንሰው ከእንቅልፉ ሲነቃ በሰገነቱ ሲመላለስ አንዲት መልከመልካም ሴትን ቢመለከት በዝሙት ጾር ተነድፏል፡፡ መነደፍ ብቻም ሳይሆን ደረሰባት፡፡ እናም አረገዘች፡፡ በኋላም ይህን ኃጢአቱ ለመሸፈን ብሎ ባሏን ጠርቶ ከእርሷ ጋር እንዲተኛና ከባሏ እንደጸነሰች ማስመሰል ፈልጐ ነበር፡፡ ኦርዮ ግን ወደ ሚስቱ ወደ ቤርሳቤህ አልሄደም፡፡ ለኦርዮ ወደ ቤቱ ሄዶ ከሚስቱም ጋር መተኛት ማለት እግዚአብሔርን (ታቦተ ጽዮንን)፣ ሕዝቡን (እስራኤልን)፣ ነገደ ይሁዳን፣ አለቃው ኢዮአብን እና በጦር ሜዳ ያሉትን ጓደኞቹን ሁሉ እንደ መሳደብ ነበረ፡፡ ዳግመኛ በመላ ፍትወቱ እንዲነሣሣበት ፈልጐ ቢያሰክረውም ኦርዮ በጌታው ምንጣፍ ከባሮቹ ጋር ተኛ እንጂ ወደ ሚስቱ አልሄደም፡፡ ከዚህ በኋላ ዳዊት ያሰበው ሁሉ እንዳልተፈጸመለት ባየ ጊዜ ኦርዮን ማስገደል መርጧል፡፡ እናም አስገደለው፡፡ መጽሐፍ ዳዊት ያደረገው ሁሉ ማለትም ከቤርሳቤህ ጋር መድረሱ፣ ይባስ ብሎም አንዱን ባሏ ኦርዮን ማስገደሉ “በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ሆነ” ይላል /2ሳሙ.11፡27/፡፡ ምንም እንኳን ዳዊት መንፈሳዊ ልምምዶችን የተለማመደ፣ ሕግ አዋቂ፣ በሕዝብ ላይ የሚፈርድ ንጉሥ፣ የእግዚአብሔርም ነብይ ቢሆንም ከዚህ ኃጢአቱ ሊመለስ ባለመቻሉ ሌላ ነብይ አስፈልጐታል፡፡ ስለዚህም ነብዩ ናታን በጥበብ ገስጾታል፡፡ ከዚህ ሁሉ በኋላ ዳዊት ያለ ምንም ማመካኘት ኦርዮን ወይም ቤርሳቤህን ሳይሆን “እግዚአብሔርን በድያለሁ” በማለት ንስሐ ገብቷል /2ነገ.12፡13/፡፡ እንዲህ በማድረጉም “እግዚአብሔር… ኃጢአትህን አርቆልሃል” ተባለ፡፡ ስለዚህ ዳዊት በግልጽ ቋንቋ አመነዘረ እንጂ ሌላ ሴት አገባ አይባልም፡፡ ለዚህም ነው ሊቃውንት “የዳዊት ቅድስና ከንስሐ እንጂ ካለመበደል የተገኘ አይደለም” የሚሉት፡፡ 4. ልጁ ሰሎሞንም ቢሆን ብዙ ሚስቶችን ቢያገባም መጽሐፍ ቅዱስ “እንዲህ በማድረጉ እግዚአብሔርን አሳዘነው” እንጂ “አስደሰተው” ብሎ አልመዘገበልንም፡፡ እንዲያውም እንዲህ በማድረጉ ዕድሜው አጥሯል፤ መንግሥቱ ለሁለት ተከፍሏል፡፡ ይህን ታሪክ በ1ነገ.11 ሙሉውን ማንበብ ይቻላል፡፡ በአጠቃላይ ከአንዲት በላይ ሚስት ማግባት ከሕገ እግዚአብሔርና ከስነ ተፈጥሮ አንጻር ተቀባይነት የለውም፡፡ ምክንያቱም ከሕገ እግዚአብሔር አንጻር ስናየው አንድ ወንድና አንዲት ሴት አድርጐ ፈጠራቸው ብቻ ሳይሆን አንድ ወንድ ከአንዲት ሴት ጋር ብቻ መተባበር እንዳለባቸውም ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ይህ ፈቃዱም ትዕዛዙም ባይሆን ኖሮ ወይም ደግሞ አንዱ ወንድ ከአንዲት ሚስት በላይ ማግባት ተፈቅዶለት ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር አስቀድሞ ለአንድ አዳም ብዙ ሴቶችን በፈጠረለት ነበር፡፡ ወይም በግልባጩ አንዲት ሴት ከአንድ ወንድ በላይ ማግባት ተፈቅዶላት ቢሆን ኖሮ ብዙ ወንዶችን ፈጥሮ ከአንዲቷ ሴት ጋር ባጣመራቸው ነበር፡፡ ነገር ግን እንዲህ አላደረገም፡፡ ስለዚህ ከአንድ ሚሰት በላይ ማግባት ይህን ሕገ እግዚአብሔር የሚጻረር ነው፡፡ ከሕገ ተፈጥሮ አንጻር ስናየው ደግሞ ባልና ሚስት አንድ አካል ናቸው፡፡ የአንድ አዳም አካል የአንዲት ሔዋን አካል ነው፡፡ ይህ የአንድ አዳም አንድ አካል ከአንድ በላይ ሚስት አገባ ማለት ግን ከአንድ በላይ ሆነ ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ፈጽሞ ሕገ ተፈጥሮን የሚጻረር ነው፡፡ ስለዚህ ከአንዲት በላይ ሚስት ማግባት በመሐመድ የተሰበከ የሰይጣን ትምህርት እንጂ እግዚአብሔር ከመጀመርያው ያዘዘው ትእዛዝ ወይም በተፈጥሮ የሰጠው አይደለም፡፡ እግዚአብሔር በብሉይም ሆነ በሐዲስ ኪዳን እንድናገባ የፈቀደልን አንዲት ሚስትን ብቻ ነው፡፡ ክርስቶስ አንድ ነው፤ ሙሽራይቱ ቤተ ክርስቲያንም አንዲት ብቻ ናት፡፡ በክርስቶስ የተመሰለው ባልም ልትኖሮው የሚገባት አንዲት ሚስት ብቻ ናት /ኤፌ.5፡23/፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር!!

Tuesday, May 1, 2012

ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የሚነሡ ጥያቄዎች- በዲያቆን ዳንኤል ክብረት


አቡነ ተክለ ሃይማኖት እና የመንግሥት ለውጥ አንዳንዶች «ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት ወደ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት የተደረገውን ሽግግር ያከናወኑት አቡነ ተክለሃይማኖት ናቸው፡፡ ይህንንም ያደረጉት ይኩኖ አምላክ የሸዋ ሰው ስለሆነ ለዘራቸው አድልተው ነው» ይላሉ፡፡ በሸዋው ይኩኖ አምላክ እና በዛግዌ ሥርወ መንግሥት ወራሹ በነአኩቶ ለአብ መካከል መቀናቀን የተጀመረው አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሐይቅበትምህርት ላይ በነበሩበት ጊዜ ነበር፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሕፃን በነበሩበት ጊዜ ከዳሞት የሚመጣው የሞተለሚያውያን ኃይል ሸዋንደጋግሞ በመውረር አብያተ ክርስቲያናትን ዘርፏል ሕዝቡንም ማርኳል፡፡ ይህ ጉዳይ የሸዋን ሕዝብ ማስቆጨቱ እና ማነሣሣቱ የማይቀርነው፡፡ በተለይም ከአኩስም የተሰደደው የሰሎሞናዊው ሥርወ መንግሥት ዘር ሸዋ መንዝ ነው የገባው ተብሎ በሚታመንበት ሁኔታ ሸዋዎችራሳቸውን ለመከላከል መደራጀት ጀምረዋል፡፡ ደቡቡ ኢትዮጵያ ከማዕከላዊው መንግሥት መቀመጫ ከሮሐ እየራቀ ሄዶ ስለነበርለይኩኖ አምላክ ጥሩ መደላድል ሆኖታል፡፡ ገድለ ኢየሱስ ሞዓ እንደሚተርከው የመንግሥትን ነገር ከይኩኖ አምላክ ጋር የተነጋገሩት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሳይሆኑ አቡነ ኢየሱስሞዓ ናቸው፡፡ ያን ጊዜ ደግሞ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በተማሪነት ሐይቅ ገዳም ውስጥ ነበሩ፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ እና ይኩኖ አምላክ በመንግሥት ጉዳይ ላይ ለመነጋገር የበቁት ይኩኖ አምላክ በሸዋ ላይ ይደርስ ከነበረው የሞተለሚጥቃት ሸሽቶ በሐይቅ እስጢፋኖስ ትምህርት ቤት ወጣትነቱን ያሳለፈ በመሆኑ ነበር፡፡ ሁለቱ ባደረጉት ስምምነት የዐቃቤ ሰዓትነትን መዓርግ ለሐይቅ ገዳም መምህር እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ይህም ማለት የንጉሡ ገሐዳዊ ግንኙነቶች በዐቃቤ ሰዓቱ በኩልእንዲፈጸሙ ማለት ነው፡፡ • የንጉሡ ደብዳቤ ወደ ሐይቅ ገዳም ሲላክ መነኮሳቱ ተቀምጠው እንዲሰሙ • ለገዳሙ የተሰጠውን መሬት የመኳንንቱም ሆነ የነገሥታት ልጆች እንዳይነኩ • ነፍስ የገደለ፣ ንብረት የሰረቀ፣ እግረ ሙቁን ሰብሮ እዚህ ገዳም ገብቶ ቢደውል ከሞት ፍርድ እንዲድን • ለገዳሙ የተሰጠው ርስት ለአገልጋዮች ብቻ ስለሆነ ዘር ቆጥሮ ማንም ተወላጅ እንዳይወርስ • የገዳሙ ርስት መነኩሴ ላልሆነ ጥቁር ርስት እንዳይሰጥ የሚሉት ታወጁ፡፡ ይህ ሁሉ ሲከናወን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሐይቅ ትምህርት ላይ ነበሩ፡፡ በኋላ ዘመን ይኩኖ አምላክ ኃይሉ እየበረታ ነአኩቶ ለአብም ግዛቱ እየጠበበ እና ኃይሉ እየደከመ ሲሄድ ከወሎ በታች ያለውን ሀገርየያዘው ይኩኖ አምላክ እና ላስታን እና ሰሜኑን የያዘው ይኩኖ አምላክ ለጦር ይፈላለጉ ጀመር፡፡ በዚህ ዘመን ነበር አቡነ ተክለ ሃይማኖትከኢየሩሳሌም የተመለሱት፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ያደረጉት ነገር ቢኖር ኃይሉ እየገነነ የመጣውን ይኩኖ አምላክን እና የወቅቱን ንጉሥ ነአኩቶ ለአብን ማደራደርነበር፡፡ ይኩኖ አምላክ ለመንገሥ ከቅብዐት በቀር የቀረው ኃይል አልነበረም፡፡ የነአኩቶ ለአብ ኃይል ደግሞ ቢዳከምም አልሞተም፡፡ሁኔታው ወደ እርስ በርስ ጦርነት እንዳይሄድ ያሰጋቸው አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሁለቱን በማደራደር ከአንድ ስምምነት ላይአደረሷቸው፡፡ • ይኩኖ አምላክ ምንም ኃይል ቢኖረው ነአኩቶ ለአብ እስኪያርፍ ድረስ ንግሥናውን እንዳያውጅ • ከነአኩቶ ለአብም በኋላ የዛግዌ ዘር የላስታን አውራጃ እንዲገዛ • የላስታው ገዥ በፕሮቶኮል ከንጉሡ ቀጥሎ እንዲሆን ይህ ስምምነት ባይኖር ኖሮ ጦር በሰበሰበው በይኩኖ አምላክ እና ሥልጣን ላይ በነበረው በነአኩቶ ለአብ መካከል በሚፈጠረው ጦርነትየሀገሪቱ ልጆች ባለቁ ነበር፡፡ ዛሬ ቢሆን ይሄ ተግባር የኖቬል ሽልማት የሚያሸልም ነበር፡፡ ይህ ስምምነት በኋላ በዐፄ ይትባረክ ዘመንበመፍረስ የተከሰተውን ጦርነት ያየ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ያደንቃል እንጂ አይተችም፡፡ ሲሦ መንግሥት አንዳንዶች «አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት በዋሉት ውለታ ለቤተ ክርስቲያን ሲሦ መንግሥት ተሰጠ» ይላሉ ይኩኖ አምላክሲነግሥ በኢትዮጵያ ውስጥ ጳጳስ አልነበረም፡፡ ከአቡነ ጌርሎስ ሞት በኋላ ከግብፅ የመጣ ጳጳስ አልነበረም፡፡ ይህ ሁኔታ በመንፈሳዊትንሣኤ ላይ ለነበረችው ኢትዮጵያ የአገልጋዮች እጥረት አስከተለ፡፡ በዚህ ጊዜ የተሰባሰቡት የኢትዮጵያ ሊቃውንት በትምህርትምበአገልግሎትም የበረቱትን አቡነ ተክለ ሃይማኖትን መረጡ፡፡ የሚሾም ሲኖዶስ አልነበረምና እግዚአብሔር «ሐዋርያትን በሾምኩበትሥልጣን ሾምኩህ» አላቸው፡፡ ይኩኖ አምላክ ምንም እንኳን በንግሥናው ቢገዛ እንደ ወጉ ሥርዓተ መንግሥት አልተፈጸመለትም ነበር፡፡ በመሆኑም በዘመኑ የነበሩትአቡነ ተክለ ሃይማኖት ሥርዓተ መንግሥቱን ፈጸሙለት፡፡ እርሱም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ርስት ሰጠ፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ርስት መስጠት በይኩኖ አምላክ የተጀመረ አይደለም፡፡ እንዲያውም ቅዱስ ላሊበላ ለአኩስም፣ ለላሊበላ፣ለመርጡለ ማርያም እና ለተድባበ ማርያም የሰጠው ርስት ይበልጣል፡፡ በወቅቱ ለሐዋርያዊ አገልግሎት እና ለተማሪዎች ድርጎ ለቤተክርስቲያን ጥሪት ያስፈልጋት ስለነበር ይኩኖ አምላክ ርስት ሰጥቷል፡፡ ይህ ግን ከመንግሥት ዝውውር ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም፡፡ዛሬም ቢሆን እኮ አንዳንድ የአውሮፓ ሀገሮች ለቤተ ክርስቲያን የተለየ በጀት ይሰጣሉ፡፡ እጨጌ የሚለውን ስም ከርስት አስተዳዳሪነት ጋር የሚያገናኙት ሰዎች አሉ፡፡ እጨጌ የሚለውን ስም ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት የሰጣቸውመንግሥት ሳይሆን የወላይታ ሕዝብ ነው፡፡ በወላይተኛ «ጨጌ» ማለት «ሽማግሌ፣ ታላቅ፣ አባት» ማለት ነው፡፡ ወደ አማርኛ ሲመጣ«እጨጌ» ተባለ፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን አገልግሎት አይቶ ይህንን የሰጣቸው ሕዝቡ ነው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሥልጣን ወዳድአለመሆናቸውን በግልጽ አሳይተዋል፡፡ ከብዙ ዘመናት በኋላ አቡነ ዮሐንስ 5ኛ ከግብጽ መጥተው አቡነ ተክለ ሃይማኖትን በግማሽኢትዮጵያ በመንበረ ጵጵስና እንዲያገለግሉ ለምነዋቸው ነበር፡፡ እርሳቸው ግን ለሥልጣን ፍላጎት እንደሌላቸው ገልጸው እንዲያ ሕዝብሲወዳቸው እና ሲፈልጋቸው ወደ በኣታቸው ነው የተመለሱት፡፡ «ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሌላ ናቸው » አንዳንዶች «በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከ8 እስከ 13ኛው መክዘ ባለው ጊዜ የኖሩ ሌላ ተክለ ሃይማኖት የሚባሉ ጻድቅ ነበሩ፡፡ የርሳቸውታሪክ ከሌላ ተክለ ሃይማኖት ታሪክ ጋር ተዳብሎ አሁን ያለWን ገድለ ተክለ ሃይማኖት አስገኘ፡፡ እናም ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስአይደሉም » ይላሉ እስካሁን ድረስ ይህንን አባባል የሚጠቅሱ ሰዎች ያቀረቡት ማስረጃ የላቸውም፡፡ እገሌ አይቶት ነበር፡፡ እዚህ ገዳም ነበር ከማለትውጭ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ለሌለ ማስረጃ ሲባል ያለ ማስረጃ አይሰረዝም፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስን በተመለከተ ያሉት ማስረጃዎች አራት ዓይነት ናቸው፡፡ 1. ገድላቸው 2. የሌሎች ቅዱሳን ገድሎች 3. ዜና መዋዕሎች እና 4. የግብፅ ቤተ ክርስቲያን መረጃዎች ገድለ ተክለ ሃይማኖት እኔ ለማየት የቻልኩት የደብረ ሊባኖስ፣ የሐይቅ እስጢፋኖስ፣ የዋልድባ፣ የጉንዳንዳጉንዲ እንዲሁም ዐፄ ምኒሊክ ወላይታን ሲወጉያገኙት የወላይታ ገድለ ተክለ ሃይማኖት ቅጂዎች አልፎ አልፎ ከሚያሳዩት መለያየት በስተቀር የሚተርኩት በ13ኛው መክዘ ስለነበሩትተክለ ሃይማኖት ነው፡፡ እኒህ ተክለ ሃይማኖት ጽላልሽ ተወልደው፣ በኢትዮጵያ ገዳማት ተምረው፣ በመላ ሀገሪቱ ሰብከው፣ ግብጽእና ኢየሩሳሌም ተሻግረው፣ ደብረ ሊባኖስን መሥርተው ያገለገሉትን ተክለ ሃይማኖት ነው የሚናገሩት፡፡ ሌላው ቀርቶ ወሎ ጉባ ላፍቶ፣ ጎንደር አዞዞ ተክለ ሃይማኖት የተገኙት ገድላትም ተመሳሳይ ታሪክ ነው የሚተርኩት፡፡ እስካሁንከኒህኛው ተክለ ሃይማኖት ውጭ ስላሉ ሌላ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የሚተርክ ገድል አልተገኘም፡፡ አለ ከመባል በቀር፡፡ የኢትዮጵያ የብራና መጻሕፍትም ሆኑ በአካል ያልተገኙት ማይክሮ ፊልሞቻቸው በተከማቹባቸው በብሔራዊ ቤተ መጻሕፍትወመዛግብት፣ በመንበረ ፓትርያርክ ሙዝየም እና ቤተ መጻሕፍት፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናት ቤተ መጻሕፍት፣በብሪቲሽ ሙዝየም እና ቤተ መጻሕፍት፣ በቫቲካን ቤተ መዛግብት እና ቤተ መጻሕፍት፣ አሜሪካ ኮሌጅቪል በሚገኘው ቅዱስ ዮሐንስኮሌጅ ያሉትን ማይክሮ ፊልሞች እና የብራና መጻሕፍት ዝርዝሮችን ብናይ ስለ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስ እንጂ ስለሌላ ተክለ ሃይማኖት የተጻፈ ገድል የለም፡፡ (የዚህን ዝርዝር የጥናት ውጤት በቅርብ ለኅትመት አበቃዋለሁ፡፡) ሌሎች ገድሎች ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የሚያነሡ አያሌ ገድሎች አሉ፡፡ ገድለ አኖሬዎስ ዘሞረት፣ ገድለ አቡነ አኖሬዎስ ዘወረብ፣ ገድለ አቡነፊልጶስ፣ ገድለ አቡነ ኤልሳዕ፣ ገድለ አቡነ ሕዝቅኤል፣ ገድለ አቡነ ዜና ማርቆስ፣ ገድለ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ፣ ገድለ አቡነቀውስጦስ፣ ገድለ አቡነ ማትያስ፣ ገድለ አቡነ ታዴዎስ ዘጽላልሽ፣ ገድለ አቡነ ገብረ ክርስቶስ ዘግድም፣ ገድለ አቡነ መርቆሬዎስዘመርሐ ቤቴ፣ ገድለ አቡነ አድኃኒ ዘዳሞት፣ ገድለ አቡነ ኢዮስያስ ዘወጅ፣ ገድለ አቡነ ዮሴፍ ዘእናርያ፣ ገድለ አባ ጊዮርጊስዘጋሥጫ እና ሌሎች ወደ አሥራ ሦስት የሚጠጉ ገድላት ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ተጨማሪ መረጃዎች ይሰጣሉ፡፡ እነዚህ ሁሉገድላት የሚያነሷቸው ተክለ ሃይማኖት ግን ተክለ ሃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስን ነው፡፡ ዜና መዋዕሎች የይኩኖ አምላክ፣ የዓምደ ጽዮን፣ የዘርዐ ያዕቆብ፣ የሱስንዮስ፣ እና የሌሎቹም ዜና መዋዕሎች ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘደብረሊባኖስ ይተርካሉ፡፡ ግብፃውያን መዛግብት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው ቅዱሳን መካከል አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንዱ ናቸው፡፡ እንዲያውምቤተ ክርስቲያንዋ የአራት ቅዱሳንን ብቻ የልደት በዓል ታከብራለች፡፡ የጌታን፣ የእመቤታችንን፣ የዮሐንስመጥምቅን እና የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን፡፡ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ጥንታውያንም ይሁኑ ዘመናውያንመዛግብት የሚገልጹት በ12ኛው መክዘ ጽላልሽ ተወልደው ስላደጉት ስለ ደብረ ሊባኖሱ አቡነ ተክለ ሃይማኖትነው፡፡ እናም ወደፊት አዲስ ነገር ተገኘ ስንባል ያን ጊዜ እንከራከር ካልሆነ በቀር እስካሁን ድረስ ግን ከአቡነ ተክለሃይማኖት ጋር የታሪክ ዝምድና ያላቸው ሌላ ተክለ ሃይማኖት መኖራቸውን የሚገልጥ ማስረጃ የለም፡፡
 ተመሳሳይ ገጾች

አባታችን ተክለሃይማኖት ማለት እኒህ ናቸው

በአቡነ ተክለሃይማኖት ገድል ላይ የሚነሱ አንዳንድ ጥያቄዎች

እግር ያለው ባለ ክንፍ

FeedBurner FeedCount