Monday, March 31, 2014

ገብር ኄር ዘሠሉስ



በዲ/ን ስመኘው ጌትዬ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ መጋቢት 22 ቀን 2006 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

 በልዕልናው ከልዑላን ይልቅ ከፍ ያለ፣ በቅድስናው ከቅዱሳን ይልቅ ቅዱስ የሆነ፣ በግርማው ከአስፈሪዎች ሁሉ የሚያስፈራ፣ በማስተዋልም የጥበበኞች ጥበበኛ ስለእርሱ መገኘቱ ከመቼ ጀምሮ ነው? አነዋወሩስ እስከመቼ ነው? ቁመቱ ምን ያህል ነው? ወርዱስ ይህን ያህል ነው፤ ራስጌው በዚያ በኩል ነው፤ ግርጌውም በዚያ በኩል ነው፤ መምጫው ከዚህ በኩል ነው፤ መድረሻውም እስከዚህ ድረስ ነው በማይባል በእግዚአብሔር ስም ሰላም ይሁንላችሁ:: (መጽሐፈ ምሥጢር)

 ነአኵቶ ለእግዚአብሔር ለዘዓቀበነ ወአንቅሐነ እምንዋም ክቡድከከባድ እንቅልፍ ላነቃን ለጠበቀን ለእግዚአብሔር ምሥጋና ይሁን:: እንደ አንተ ይቅር ባይ ማነው? በሰማይና በምድር ይገድላል፤ ያድናል፤ ይቤዣል፤ ያድናል፡፡ ዳዊት እንዳለ እግዚአብሔር ያበራልኛል፤ ለሕይወቴም መጠጊያዋ ነው::” ይህ የዕለት የጠዋት ምግባችን ነው:: በተለይ ደግሞ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን በጠዋት ቀናችንን በቡና ሳይሆን በጸሎት ለምንጀምር የቅዱስ ያሬድ የጠዋት ምሥጋና የሕይወታችን ክፍል ሊሆን ይገባል::

 ዕስየኒ እግዚኦ ሠናይተከ ኅሥዋ ለጽዮንአቤቱ መልካምነትን ስጠኝ፡፡ ጽዮንን ፈልጔት፤ መንገዷንም ተከተሉ፡፡ መንገዷን ጠብቁ፡፡ ሕጔን የጠበቀ ያገኛል፤ ቤተክርስቲያንን የወደዳት አይደክምም፡፡ እንደ እናቱ ታቅፈዋለች፤ ከወንድሞች ይልቅ ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤ የጥበብ እና የዕውቀት ምግብን ትመግበዋለች፤ ፍጹም የደስታን አክሊል ታቀዳጀዋለች:: አቤቱ መልካምነትን ስጠኝ፡፡ ጉስቁልና የሌለበትን ሕይወት እና በጎነት::” እንግዲህ ሊቁ በዜማ በጠዋት የሚያመሰግናት ጽዮን ቤተክርስቲያን ስለእርሷ ክብር ሳይሆን እርሱ የሚያመሰግናት ይከብር ዘንድ ነው:: ጽዮን ሆይ አልረሳሽም እንድንል ይመክረናል::

 አንትሙሰ ጸልዩ ሶበ ትጸውሙእናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ ጸልዩ፤ አትጠራጠሩ፤ ሁሉን መርምሩ፤ በሁሉም ጊዜ በመፋቀር ኑሩ::” የጾምና የጸሎት መድረስ የሚረጋገጠው በሕይወታችን በሚንጸባረቀው ፍቅር ነው:: ፍቅር ከሌለን ጾምና ጸሎታችን የሥጋ ድካም ብቻ ይሆንብናል:: ለዚህም ነው ዜመኛው ስለፍቅር በየገጹ የሚናገረው::

 ንጹም ጾመ ወናፍቅር ቢጸነጾምን እንጹም፤ ወንድማችንን እንውደድ፡፡ እርስ በርስም እንዋደድ:: በችግራችን ጊዜ እንደዚህ የሚረዳን እንደዚህ የሚጠቅመን ምንም የለም፤ የቤታችን ክብር (ሃብታችን) ሁሉ ከእኛ ጋር አይወርድም፤ ዓለሙም ምኞቱም ሃላፊ ነው፤ ለነፍስ ድኅነት የሚሆን አይደለም:: የሰማይ ማደሪያችሁን ፈልጉ::” በጾም ጊዜ ፍቅር አንድነት አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን መንግሥቱን ለሚጠብቅ ሰው ግዴታውም ነው::

 አኃውየ ቀድሱ ጾመወንድሞቼ ጾምን ቀድሱ፤ ምሕላንም አስተምሩ፤ ሰላምን አድርጉ፤ ሐዋርያው በክርስቶስ ያላችሁ ሁላችሁ ተስማሙ ተስማሙ ተስማሙ እንዳለው::” ቅዱስ ያሬድ ምክሩን ይቀጥላል፡፡ በዚህ ባለፈው በሚመጣውም የጾም ወቅት በቃሉ ራሳችንን እንለካ እንመርምር:: በእውነት የሚገባ ጾም ጾምኩን?

 ሠናየ ሐልዩ ለቢጽክሙለወንድማችሁ መልካም አስቡ፤ በሁሉም ጊዜ ተፋቀሩ፤ የእግዚአብሔር ፈቃድ ይህ ነውና መንፈሱን አታጥፉ፤ ትንቢትንም አትናቁ፤ ሁሉን መርምሩ፤ በጎውን አጽኑ::” በበጎ ውስጥ ሁሉ እርሱ አለ:: በበጎ የምትለምኑትን ይለናል ቅዱስ ያሬድ ይሰማችኋል፤ ገና ስታስቡት ምኞታችሁን ይፈጽምላችኋል::

 “…ጾም ቅድስት ይእቲ ታድኅን እሞት ታስተፌስሕ በሰማያትጾም ቅድስት ነች፡፡ ከሞት ታድናለች በሰማያት ታስደስታለች::” የሰማዩን ሰላምና ደስታ ይስጠን::

No comments:

Post a Comment

FeedBurner FeedCount